Thursday, June 25, 2009

 

እኛም የዲሞክራሲ ጀግኖች አሉን !

ግርማ ካሳ (muziky68@yahoo.com)

















ግርማ ካሳ (muziky68@yahoo.com)

ሰኔ 29 ቀን 2001

ኔዳ አጋ ሱልጣን ትባላለች። በቅርቡ የተደረገዉን የምርጫ መጭበርበር በተመለከተ በኢራን በተደረገዉ ሰላማዊ ሰልፍ ከደህንነት አባላት በተተኮሰ ጥይት የተገደለች ናት። ከቤቷ ስትወጣ የወጣችዉ ድምጿ እንዲከበርላት፣ የሰብዓዊ መብቷ እንዲረጋገጥ በሰላም ነበር። በሕይወቷ ማከናወን የምትፈልጋቸዉ ብዙ እቅዶች ይኖሯታል። ነገር ግን እቅዶቿን ሁሉ ትታ ወደቀች። ተገደለች።

ኔዳ የዲሞክራሲ ምልክት ሆና በአለም ሁሉ ስለእርሷ እየተነገረ ነዉ። በኢራን የዲሞክራሲ ታጋዮች ዘንድ፣ በሥጋዋ ከዚህ አለም ብትለይም፣ በኢራን የዲሞክራሲ ትግል ታሪክ ዉስጥ ግን ልዩ ቦታ ይዛለች። የሞተችበት አላማም በሕዝቡ ዉስጥ ማእከል ቦታ ይዞ እየተቀጣጠለ ነዉ።

እኛ አገር ተመሳሳይ ሁኔታ ከአራት አመታት በፊት አይተናል። አሁን በሥልጣን ላይ ያለዉ የኢሕአዴግ መንግስት በምርጫ ከፍተኛ ሽንፈት ሲደርስበት፣ ኮረጆ መቀያየር ጀመረ። ሳያሸንፍ አሸንፊያለሁ ብሎ አወጀ። የምርጫዉን መጭበርበር፣ በኢራን አሁን እየተደረገ እንዳለዉ፣ ሕዝብ ሰላማዊ ሰልፍ በመዉጣት ተቃወመ። በአቶ መለስ ዜናዊ የሚመራዉ የአጋዚ ጦርና የፌደራል ፖሊሲ ትልቅ ጭካኔ የተሞላበት የኃይል እርምጃ ወሰዱ። በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰላማዊ ዜጎችን ገደሉ።

የዚያን ጊዜ ነበር የአሥራ ስድስት አመቷ ወጣት፣ የኛ «ኔዳ» የሆነችዉ፣ ሽብሬ ደሳለኝ ለዲሞክራሲና ለነጻነት ስትል የተገደለቸዉ። አለም ስለርሷ አልዘገበም። ሲኤንዔን፣ ቢቢሲ ዋሺንግተን ፖስትና ኑዮርክ ታይምስ ፎቶዎቿን አላወጡም። የምእራባዉያን አገሮች ተቃዉሟቸዉን አላሰሙም። ብዙዎች አያዉቋትም። ነገር ግን እኛ እናዉቃታለን። በኛ ዘንድ ግን የተረሳች አይደለችም።

ይሄን ጊዜ ሽብሬ ደሳለኝ ሃያ አመት ይሆናት ነበር። ምናልባትም የዮኒቨርሲቲ ተማሪ ልትሆን ትችል ነበር።

ገዳዮቿ ሊረሱ ይችላሉ። ከአራት አመት በፊት የሰሩትን ግፎች ከዚያ በኋላ እየደጋገሙ ስለፈጸሙ ብዙ ያስታዉሱታል ብዬ አላስብም። ነገር ግን አንድ የምናዉቀዉ ነገር አለ። ሽብሬ ደሳለኝ መቼም ቢሆን አትረሳም። እስከ አሁን ድረስ የሕሊና ጆሮ ላለዉ ሰዉ፣ የፈሰሰዉ ደሟ ሲጮህ ይሰማል። አሁንም ሽብሬ ደሳለኝ ትጣራለች። አሁንም መልእክቶቿ እየደረሱን ነዉ።

«ትግሉን ተቀላቀሉ። በአገራቹህ ጉዳይ ላይ ባይተዋር አትሆኑ። ከሌሎች ህዝቦች ተማሩ። ሌላዉ ሲጠቃ ዝም የሚል የፈሪ ባህልን አስወግዱ። እኛ ደማችንን ያፈሰስንበትን አላማ ከግቡ አድርሱት።» ትለናለች።

እነ በርቱካን ሚድቅሳ የሽብሬን ጥሪ ተቀብለዉ የጨካኞችን ግፍ እየተቀበሉ ነዉ። ለእዉነትና ለሐቅ በመቆም፣ ማስፈራሪያንና ዛቻን በመናቅ እርሳቸዉን ሰውተዉ ደረታቸዉን ለጥይት አሳልፈዉ ሰጥተዋል።

እኛስ ? መልሳችን ምንድን ነዉ ?

Wednesday, June 24, 2009

 

ኢትዮጵያ ጽጌሬዳችን ናት !

በግርማ ካሣ
ቺካጎ (muziky68@yahoo.com)

ኢትዮጵያን በጽጌረዳ አበባ እመስላታለሁ። ጽጌሬዳ አበባ በጣም ተወዳጅ የሆነች አበባ ናት። ብዙ ጊዜ በማስቀመጫ ዉስጥ ተደርጋ የሚመጡ እንግዶች እንዲያይዋት በሚታይ ቦታ ትቀመጣለች። የክብር የፍቅርና የዉበት ምልክት ናት። ኢትዮጵያ አገራችንም በነጻነቷና በአንድነቷ ታፍራና ተክብራ የኖረች፣ ከተለያዩ ብሄረሰቦች የተወጣጡ ልጆቿ ዉበቷ የሆኑላት፣ ለኢትዮጵያዉያን ብቻ ሳይሆን ለጥቁር ህዝብ ሁሉ ኩራት የሆነች አገር ናት።

የቀድሞዉ የደቡብ አፍሪካ ፕሬዘዳንት ኔልሰን ማንዴላ ሰለ ኢትዮጵይ ሲናገሩ “ኢትዮጵያ በሐሳቤ ልዩ ቦታ አላት፤ ኢትዮጵያን መጎብኘትም ፈረንሳይ እንግሊዝንና አሜሪካን ከመጎብኘት የበለጠ ይስበኛል” ይሉናል። ስለ ዳግማዊ አጼ ሚኒሊክ አንድ በተባበሩት መንግስታት ጽ/ቤት የኢኮኖሚክ ኮሚሽን ፎር አፍሪካ ከፍተኛ ባለስልጣን የነበሩ፣ ሴኔጋላዊ ከ አሥራ ሰባት አመታት በፊት የነገሩኝ ቁም ነገር ነበር። “ስለ አጼ ሚኒሊክና የአድዋዉ ጦርነት የሴኔጋል ተማሪዎች ይማሩታል። የአድዋዉ ድል የአፍሪካ የነጻነት ምዕራፍ ጅማሬ ነዉ። ሚኒሊክ የኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን የአፍሪካ አባት ናቸዉ” ሲሉ ነበር ኢትዮጵያ በሴነጋል ተወላጆች ዘንድ ያላትን ልዩ ቦታ በግልጽ ያስቀመጡልኝ። አዎ ኢትዮጵያ የኛ የኢትዮጵያዉያን ብቻ ሳይሆን የጥቁር ሕዝብ ሁሉ ጽጌሬዳ ናት።

ኢትዮጵያ እንዲህ ለጥቁር ሕዝብ ሁላ ኩራት የሆነችዉ በቀላሉ አይደለም። የኢትዮጵያን ነጻነትና ክብር ለማስጠበቅ የተከፈለዉ መስዋዕትነት እጅግ በጣም ትልቅ ነዉ።

በአድዋ፣ በማይጨዉ፣ በአዱሊስ በወልወልና በመላዉ የኢትዮጵያ ግዛት ከወራሪ ጣሊያኖች ጋር፤ በጉንደትና በጉራ ከግብጾች ጋር፤ በአፋር ምድር ከቱርኮች ጋርና እንዲሁም “ታላቋ ሶማሊያ” በሚል መርህ የተሰማራዉን የዉጭ ወራሪ ኃይል ለመመከት በሃረርጌ በተደረጉት ታላቅ ትንቅንቆች ትቅል የደም መስዋዕትነት ተከፍሏል።

በመተማ ከደርቡሾች በተተኮሰ ጥይት ያለፉትን አጼ ዮሐንስ አራተኛ፣ በመቅደላ ተራራ ለኢትዮጵያ ክብር ሲሉ እጃቸዉን ለእንግሊዞች ላለመስጠት የራሳቸዉን ጥይት የጠቱትን መይሳዉ አጼ ቴዎድሮስን ፣ የዘርዓይደረሰን፣ የአብዲሳ አጋን፣ የደጃች ባልቻ አባነፍሶን፣ የፊታዉራሪ ገበየሁን፣ የጥቁር አንበሳ ጀግኖችንና እንዲሁም በተለያዩ አጋጣሚ ለኢትዮጵይ ነጻነትና ክብር ሲሉ ህይወታቸዉን ሰዉተው ያለፉ ወገኖቻችንን ቁጠር እጅግ በጣም ብዙ ነዉ።

ጽጌሬዳ መልከ መልካምና ያማረች የሆነችዉን ያህል የሚዋጉና የሚያደሙ እሾሆችም አሏት። በአዲስ አበባ፣ በሃዉሴን፣ በአሲምባ፣ በከረን፣ በአስመራ፣ በአሶሳ፣ በጎንደር፣ በኦጋዴን፣ በምዕራብ ወለጋ፣ በበደኖ፣ በአርባ ጉጉ … በእሾህ ተወግቶ የስንቱ ኢትዮጵያዊ ደም ፈሰሰ ? ስንቱ በወንድሙ እጅ ታረደ ? የስንቱ ወጣት እናት ልጇን አጣች?


በአገራችን ለዘመናት በነበረዉ የእርስ በርስ ጦርነት ያለቁት ወንድሞቻችንና እህቶቻችን ተምረዉ፣ ትዳር ይዘዉ፣ ልጆች ወልደዉና ከብረዉ ለወግ ለማዕረግ መድረስ የሚችሉ ነበሩ። አሁን በሕይወት እንዳለን እንደ ማናችንም አንዳንዶቹ ሀኮሚች፣ አንዳንዶቹ መሃንዲሶች፣ አንዳንዶቹ ምሁራን፤ አንዳንዶቹ የሕግ ባለሞያዎች ሆነዉ ህብረተሰባቸዉንና አገራቸዉን ሊጠቅሙ የሚችሉ ነበሩ። ታዲይ ምን ያደርጋል የኢትዮጵያ ኋላ ቀር የደም መፋሰስና የመገዳደል ባህል ሰለባ ሆነዉ ቀሩ።

በአኩሪ ታሪካችን እንደምንኮራዉ ሁሉ በአሳፈሪዉ ታሪካችንም ማፈር አለብን እላለሁ። አገር እያለን ተሰደናል። ወገን እያለን ብቸኞች ሆነናል። ለሌሎች አገሮች የተረፈ ታላላቅ ወንዞች እያሉን ተጠምተናል። ምግብ እያለን ተረበናል። የአገራችን መሬቶች በደም ከመራሳቸዉ የተነሳ እህል ማብቀል አቁመዉ ከአመት እሰከ አመት ለህልዉናችን የፈረንጆችን እጅ እየጠበቅን ኖረናል። (ስንዴና እሩዝ ዘይትና ብስኩት እየለገሱን)

ታዲያ ለዚህ ሁሉ መከራና የሰቆቃ እሽክርክሪት ተጠያቂዉ ማን ሊሆን ይችላል ? አንዳንዶቻችን በአገራችን ለተፈጠረዉ ችግርና መከራ እጆቻችንን መንግስት ላይ እንቀስራለን። በንጉሱ ዘመን የዓጼ ሃይለስላሴ ቀዳማዊን አገዛዝ ስንረግምና ስንቃወም አብዮቱ ፈነዳ። “ኢትዮጵያ ትቅደም ያለ ምንም ደም” ተብሎ ተለፈፈብን። ወታደራዊዉ መንግስት ዙፋኑን በልጆቻችን አስክሬን ላይ ሰርቶ ገዛን። ከዚያም ቁምጣ የታጥቁ፣ “ከደርግ ብሶት የተወለድን ነን” የሚሉ “ነጻ ልናወጣችሁ፣ ዲሞክራሲ ልናመጣላችሁ ነዉ” አሉን። የከተሞቻችንን በሮች ከፍተን አስገባናቸዉ። ብዙም የተሻለ ነገር አልመጣም። አገር ወደብ አልባ ሆነች። ሃብት በጥቂቶች ተመዘበረ። ህዝብን በጎሳና በዘር ለመከፋፈል ተሞከረ። በዲሞክራሲ ስም ከአንድ በመቶ በታች የሆኑት ጨረቃ ላይ ሲመጠቁ ዘጠና ዘጠኝ በመቶ የሆነዉ ህዝባችን ቁልቁል ወረደ። ለሰላምና ለፍትህ የቆሙ ለወራት ጨለማ ቤት ይበግፍና በጭካኔ ይታሰራሉ። የፍርድ ቤት ትእዛዝ አይከበርም።

አዎን - በኢትዮጵያ ለተፈጠረዉ ችግር ዋነኛዉ ምክንያት የመልካም አስተዳደር ጉድለትና የህግ የበላይነት አለመኖር መሆኑ ሳይታለም የተፈታ ጉዳይ ነዉ።

ነገር ግን በዚህ ጽሁፌ ከመንግስት ሌላ መጠየቅ ያለበት አካል እንዳለ ለማሳየት እሞክራለሁ። ይህም አካል እኔና እናንተ ነን። እያንዳንዳችን ለኢትዮጵያ አገራችን ድህነትና መቆርቆዝ በርግጥ ተጠያቂ እንደሆንን ማወቅና መቀበል ይኖርብናል። ሁላችንም መጠኑ ይለያያል እንጂ አገራችንና ወገናችንን ጎድተናል። ጥይት ላንተኩስ እንችላለን። ነገር ግን ወንድሞቻችን ሲገደሉ ዝም ማለታችን እራሱ ተጠያቂ ያደርገናል።

በአገራችን እኮ ነፍሰ ገዳይና ጨቋኝ የሚበዛዉ እኛ ስለምንፈቅድላቸዉ ነዉ። በጥቅም ይገዙላን፣ ያስፈራሩናል ከዚያ ለፍቃዳቸዉ ሕሊናችንን ሸጠን እንገዛለን። በኛ ላይ ቆመዉም በአገራችን ላይ ግፍ ይፈጽማሉ። ስለዚህ አሁን ያለዉን አገዛዝ ብቻ ከመርገም ይሄንን አገዛዝ የፈጠርነዉንና እንዲኖር ያደረግነዉን እኛኑ እርሳችንን እንውቀስ።

መተሳሰብና መደጋገፍ እንደሚያስፈልግ ለማስረዳት፡ “አሁን አንድ ኢትዮጵያዊ ጂንስ መልበስ አለበት ? ካኪ አይለብስም ። ዊስኪስ መጠጣት አለበት ? ጠጅ አይጠጣም” ብሎ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የኢንጂነሪንግ ፕሮፌሰር የነበረ አንድ ምሁር ከ አሥር ሶስት አመት በፊት የተናገረዉ ቁም ነገር ትዝ ይለኛል። ብልጽግና፣ ሃብትና መሻሻል መልካም ነገር ነዉ። ግን ከራሳችን አልፈን የወደቀዉን ሌላዉ ኢትዮጵያዊ ወገናችንን ለማንሳት እጆቻችን አጥረዉ ካልተዘረጉ ይህ የሞራል ዉድቀት ነዉ።

በሰሜን አሜሪካ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ኢትዮጵያዊያን ይኖራሉ ተብሎ ይገመታል። በህግ አንድ ሰራተኛ በሰዓት ከ 7$ በታች አይከፈለዉም። በጣም ዝቀተኛ ደሞዝ አገኘ ቢባል አንድ ሰዉ ቢያንስ በአመት 15000$ ያገኛል ማለት ነዉ። የካናዳ ወይንም ለአሜሪካ መንግስት ቢያንስ 15% (2500$ በአመት) ግብር ያስከፍላል። በሺህ የሚቆጠሩ የተማሩ ከ50 ፣ ከ70፣ ከ100 ሺህ በላይ የሚያገኙ ኢትዮጵያዉያን አሉ። በንግዱ ሥራ ተሰማርተዉ የከበሩና በርካታ ሱቆችና ኢንቨስትመንቶች ያሏቸዉም የሚናቁ አይደሉም።

እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ በቀን አንድ ዶላር ለኢትዮጵያ ቢለይ በአመት 365 ሚሊዮን ዶላር ይደርሳል። በዚህ ገንዘብ በአየር ጠባይ መለዋወጥ በየጊዜዉ ለረሃብ የሚጋለጠዉን ወገናችንን የፈረንጆችን እጅ ሳንጠብቅ ማዳን እንችል ነበር። ታዲያ አሁንም የነጮች ጥገኛ መሆናችን መንፈሳዊ ክስረታችንን አያሳይምን? በአገራችን ላለዉ ድህነት ተጠያቂዎች አያደርገንምን ? ለካናዳና ለአሜሪካ 15% ከከፈልን ወገኖቻችንን ከረሃብ ለማዉጣትና ኢትዮጵያ በረሃብ ምሳሌነት እንዳትጠቀስ ለማድረግ ከደሞዛችን ከ 0.3 % በታች መክፈል ያቅተናል? ለልመና በጂ-20 በጂ-ስምንት ስብሰባ መጋበዝ የሚያኮራና አንበሳ የሚያሰኝ ነዉ ?

እኛ ኢትዮጵያዉያን ከቻይናዎች፤ ከጃፓኖችና ከነጮች በምን እናንሳለን ? አገራችንስ የተፈጥሮ ሃብት ከማናቸዉም ባላነሰ መልኩ እግዚአብሄር የቸራት አይደለችምን ? በአለም የተደነቁ ምሁራን፣ ሳይንቲስቶች፤ የሕግ ባለሞያዎች፣ መሃንዲሶች፣ ሃኪሞች ያሏት አገር ሆና ኢትዮጵያን ከድህነቷ ማንሳትና መቀየር እንዴት ያቅተናል?

መልሱ “አያቅተንም” ነዉ። ከቃሊቲ እሥር ቤት እንደተፈቱ አንድ ወቅት ዶ/ር በፈቃዱ ደግፌ በስዊድን ለሚገኝ የሬዲዮ ጣቢያ የተናገሩት አንድ አባባል ነበር። “ኢትዮጵያን የተቸገሩና የተጨቆኑ ከእርሷ የሚሸሹ ሳይሆን ወደ እርሷ የሚሸሹ እናደርጋታለን፤ ይቻላል” ነበር ያሉት። እዉነታቸዉን ነዉ። ኢትዮጵያን የአፍሪካ ጃፓን ማድረግ ይቻላል። የሚያስፈልገዉ አንድ ነገር ብቻ ነዉ። እርሱም ፍቅርና መተሳሰብ ነዉ።

ሐዋርያዉ ቅዱስ ጳዉሎስ ለቆሮንቶስ ሰዎች በጻፈዉ መልእክቱ የፍቅርን ትርጉም ይሰጠናል።“ፍቅር ይታገሳል፣ ቸርነትንም ያደረጋል፤ አይቀናም አይመካም አይታበይም፤ ፍቅር የማይገባዉንም አያደረግም፣ የራሱንም አይፈልግም፤ ፍቅር አይበሳጭም በደልንም አይቆጥርም፤ ከእዉነት ጋር ደስ ይለዋል እንጂ ሰላ አመጻ ደስ አይለዉም ..” በማለት በዝርዝር አስተምሯል።

ፍቅር ካለን አንዳችን በአንዳችን ላይ በበቀል በእልህና በጭካኔ አንነሳም። ፍቅር ካለን ያለፈዉን መጥፎ ታሪካችን ላይ ብቻ “እኝ” ብለን ልባችንን ለእርቅና ለይቅርታ አንዘጋም። ፍቅር ካለን በወንድማችን እሬሳ ላይ እየተረማመድን በደም የተገኘ ሃብት አናከማችም። ፍቅር ካለን ጎንበስ ብለን የወንድማችንን እግር እናጥባለን እንጂ በባዶ ትዕቢት አንሞላም። ፍቅር ካለን ያለችንን አንድ ዳቦ ግማሹን ቆርሰን ለተራበዉ ወንድማችን እናካፍላለን። ፍቅር ካለን በሚሊዮን የሚቆጠር ወገናችን የሰቆቃ እንባ እያለቀሰ በዳንኪራና በጨዋታ ንዋያችንን አናጠፋም። ፍቅር ካለን ያለፈን ክስ በመምዘዝ ሰላምዊ ሰዉን በጨለማ ቤት ዉስጥ በግፍና በጫካኔ አናስረም።

“ፍቅር ከወዴት ትመጣለች ?” የሚል ጥያቄ ሊጠየቅ ይችላል። መልሱ ግልጽና ቀላል ነዉ። ፍቅር የፍቅር አምላክ ከሆነዉ ከእግዚአብሄር ዘንድ ብቻ ትገኛለች። መጽሐፍ እንደሚል እግዚአብሄር እራሱ ፍቅር ነዉ።

አሜሪካኖች አገራቸዉን የመሰረቱት በእግዚአብሄር ላይ ነዉ። የሚጠቀሙበትን ገንዝብ አገላብጠን ብንመለከት እንኳን ”በእግዚአብሄር እናምናለን” የሚለዉ አረፍተ ነገር ተጽፎበታል። በእርሱ ላይ ተመስረተዋልና እግዚአብሄርም ባረካቸዉ።

እኛ ኢትዮጵያዊያን በጣም ሃይማኖተኞች ነን። ነገር ግን ሃይማኖተኝነታችን ብዙዉን ጊዜ በዉጭ ብቻ ነዉ። መንፈሳዊ አባቶቻችን በአንድ ጎን እየተራገሙና እየተወጋገዙ ሰጋ ወደሙን ይዘዉ ይቀድሳሉ። “ይህ ህዝብ በከንፈሩ ያከበረኛል ፤ ልቡ ግን ከእኔ የራቀ ነዉ” ተበሎ እንደተጻፈ በከንፈራችን እንጂ በልባችን እግዚአብሄርን አልፈለግነዉም። በከንፈራችን ፍቅርን እናወራለን ልባችን ግን በጥላቻና በቂም የተሞላ ነዉ። ታዲያ እግዚአብሄር እንዴት አደርጎ ይታረቀን ?

እግዚአብሄር ሊባርከን፣ ሊያድሰንና ሊጎበኘን የታመነና ጻድቅ ነዉ። በግላችን በቤተሰባችንና በአገራችን መጀመሪያና ተቀዳሚ ካደረግነዉና “በእግዚአብሄር እናምናለን” የሚለዉን ቃል በልባችን ካተምን የፍቅር መንፈስ በምድራችን ይፈልቃል። ፍቅሩም እንድንተቃቀፍ፤ እንድንሳሳም፤ እንድነሸካከም ያደርገናል።

እኛ የአስተሳሰብ ለዉጥ ካደረግን፣ ከራሳችን ያለፉ ሥራዎችን ለመሥራት ከወሰንን፣ ከታጠርንበት ግላዊ የአስተሳሰብ መአቀፍ ከወጣን፣ በርሳችን ከተማመንን በጋራ በአንድነት መለወጥ የማንችለዉ ነበር የለም። ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳንና ሌሎች የሕሊና እሥረኞችን ማስፈታት እንችላለን። በኢትዮጵያ የምንፈልገዉን የዲሞክራሲ ሥርዓት መገንባት አገራችንንም ከድህነት ማወጣት እንችላለን።

Tuesday, June 23, 2009

 

የታሰሩትስ አቶ መለስ ናቸዉ - በክፋትና በጭካኔ !

ግርማ ካሳ (muziky68@yahoo.com)


ሁለቱም በኢትዮጵያ እየተፋፈመ በመጣዉ የፖለቲካ ሂደት ዉስጥ ትልቅ ስፋራ አላቸዉ። ሁለቱም አባል የሆኑበት ደርጅት ሊቀመንበር ናቸዉ። ሁለቱም በደጋፊዎቻቸዉ ይደነቃሉ። ሁለቱም የሁለተኛ ደረጅ ተማሪ የነበሩ ጊዜ ጎበዝ ተምሪዎች ነበሩ። ሁለቱም የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተማሪ ሆነዋል። ሁለቱም የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸዉን ያጠናቀቁት በአዲስ አበባ ነዉ። ሁለቱም ወላጆች እንደመሆናቸዉ የልጅን ፍቅር ያወቃሉ። ሁለቱም ኢትዮጵያዉያን ናቸዉ።

የመጀመሪዉ አቶ መለስ ዜናዊ ይባላሉ። የአምሳ አራት አመት አዛዉንት ናቸዉ። እናታቸዉ የአዲቋላ (ኤርትራ ተወላጅ) ሲሆኑ አባታችዉ ደግሞ የአድዋ ትግራይ ሰዉ ነበሩ። ሌላኛዋ ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ ናቸዉ። አባታቸዉ የወለጋ ሰዉ ሲሆኑ እናታቸዉ ደግሞ የሸዋ ሰዉ ናቸዉ።

በነዚህ ሁለት የፖለቲካ ሰዎች ዉስጥ ትግራይ፣ ኤርትራ፣ ወለጋና ሸዋን እናያለን። (ከቀድሞ የኢትዮጵያ አሥራ አራቱ ክፍለ ሃገራት አራቱ ማለት ነዉ)

አቶ መለስ ወላጆቻቸዉ ያወጡላቸዉ ስም ለገሰ የሚል ነበር። «ዜናዊ» ማለት ዜና አብሳሪ ማለት ይመስለኛል። ወላጆቻቸዉ ለገሰ ዜናዊ ሲሏቸዉ «የሚያበስር ተሰጠን፣ ተወለደልን፣ ተለገሰን» ብለዉ ሳይሆን አይቀርም ብዬ አስባለሁ። መቼም ወላጆቻቸዉ ያኔ የተመኙት አቶ መለስ(ለገሰ) መልካም ብሥራት፣ መልካም ወሬ እንዲያብሰሩ ይመስለኛል።

ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ ስማቸዉ እንደሚገልጸዉ፣ ወላጆቻቸዉ «ያማረች፣ የጣፈጠች፣ በሰዉ የተወደደች ትሁን» ብለዉ ይመስላል ብርቱካን ያሏቸዉ። «ሚደቅሳ»ም ተመሳሳይ ትርጉም አለዉ። «ሚደቅሳ» በኦሮምኛ ማሳመር፣ ማስዋብ ማለት ነዉ።

የወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳም ሆነ የአቶ መለስ ዜናዊ ቤተሰቦች ሁለቱም ልጆቻቸዉ ትልቅ ደረጃ ደርሰዉ፣ መልካም ነገር አድርገዉ፣ በመልካም ነገር ታዉቀዉ እንዲያልፉ ፍላጎት እንደነበራቸዉ ነዉ እንግዲህ የምናየዉ።

የነዚህ ሰዎች መመሳሰል እዚህ ላይ ያበቃል። አሁን ባለንበት ሁኔታ አቶ መለስ ዜናዊ ትልቅ ጭካኔ የተሞላበት ኢሰብአዊ ሥራ በሰላማዊ ዜጎች ላይ እስኪሰሩ ድረስ በጥላቻና በክፋት የተሞሉ እልኸኛ ሰዉ እንደሆኑ እያሳዩ ናቸዉ።

ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ «ቅንጅት የሰዉ ጠላት የለዉም። ወያኔ ጠላት አይደለም። ለአገራችን መፍትሄ ፍቅር ነዉ። ያሰሩኝን ይቅር ብያለሁ» እስከማለት ድረስ በፍቅርና በደግነት የተሞሉ፣ የበደሏቸዉንና ወደ ሁለት አመት ገደማ በግፍ ያሰሯቸዉን ሰዎች ይቅር ያሉ ሰዉ ናቸዉ። አንድ ልዩነት በሉልኝ።

አቶ መለስ ዜናዊ በሚቆጣጠሩት የደህንነት ጽ/ቤት፣ የፌደራል ፖሊስና የአጋዚ ጦር ይመካሉ። እነዚህን ሕሊና የለሽ ሰዎች በመላክ በመቶ የሚቆጠሩ ዜጎችን በጠራራ ጸሃይ አስገድለዋል። በመቶ ሾህ የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያንን በግፍ አሳስረዋል። ሰላማዊ መንደሮችን እንዲቃጠሉ አስደርገዋል።
ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ የታጠቀ ሰራዊት የላቸዉም። በቤታቸዉ መሳሪያ አልተገኘም። በእጆቻቸዉ የወደቀዉን ያነሳሉ እንጂ የቆመዉን ተኩሰዉ አይጥሉም። የሚተማመኑት በሕዝብ ጉልበት እንጂ በጠመንጃ አይደለም። ሁለተኛ ልዩነት በሉልኝ።

አቶ መለስ ዜናዊ በተደጋጋሚ እርሳቸዉንና ደጋፊዎቻቸዉን ትዝብት ዉስጥ እስኪከቱ ድረስ የሚዋሹ ቀጣፊ ሰዉ ናቸዉ። ለምስሌ የቅንጅት መሪዎች ከሁለት አመታት በፊት በተፈቱ ጊዜ አቶ መለስ « ከአሁን በኋላ ወደ ፊት እንጂ ወደ ኋላ መመለስ የለብንም። ሕግን እስካልጣሱ ድረስ (የተፈቱት እሥረኞች) ሙሉ የፖለቲካ መብታቸዉ ተጠብቆ መንቀሳቀስ ይችላሉ» ነበር ያሉት። ነገር ግን ታሪካቸዉን ለዉጠዉ፣ ቀድሞ ከተፈቱት እሥረኞች መካከል ወ/ት ብርትካን ሚደቅሳ በግፍ እንድትታሰር ፈቅደዋል።

ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ ያላደረጉትን «አድርጊያለሁ» እንዲሉ፣ እንዲዋሹ ግፊትና ዛቻ ቢደረግባቸዉም «እምቢ» ብለዉ ለእዉነት የቆሙ ሰዉ ናቸዉ። ለእዉነትም በመቆማቸዉ ትልቅ ዋጋ በአሁኑ ወቅት በመክፈል ላይ ይገኛሉ። ሶስተኛ ልዩነት በሉልኝ”አቶ መለስ ዜናዊ ከቀድሞ የ66ቱ አብዮት ዘመን ከነበረዉ፣ እርስ በርስ በደም ከተቃባዉ ፣ እምነተ ቢስ ፍልስፍናን ለኢትዮጵያ ህዝብ ካስተዋወቀዉ፣ አገራችንን ወደ ጨለማ ከወሰደዉ ትዉልድ ናቸዉ። ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ በጥላቻና በቂም በቀል ካልተሞላዉ ከአዲሱ ትዉልድ ናቸዉ። አራተኛ ልዩነት በሉልኝ !

ምንም ቢሆን ክፉ የሰራ ሰዉ በመንፈሱ ሰላም ስለማያገኝ ፣ አቶ መለስ ዜናዊ የጭንቀትና የመንፈስ ረብሻ፣ የፍርሃት እሥረኛ ሆነዉ እየተሰቃዩ ናቸዉ። እራሳቸውን ይፈራሉ። አብረዋቸዉ ያሉትን የፖሊት ቢሮ አባላት ይፈራሉ። ህዝቡን ይፈራሉ። (ምናልባት የማይፈሩት ጎርደን ብራዉንና ሲልቪዮ ቤሎስኮኒን ብቻ ሳይሆን አይቀርም።) ሌሊት፣ በቤተ መንግስትም በላጠጠ መኝታ ላይ እየተኙ እንቅልፍ የላቸዉም። ለዚህ ሳይሆን አይቀርም ነገሮችን ለመርሳት ያስችል ዘንድ ሲጋራና ጫት አረቄና ካቲካላ የአራት ኪሎን ቤተ መንግስት የሞላዉ። አላወቁትም እንጂ የታሰሩትስ አቶ መለስ ዜናዊ እራሳቸዉ ናቸዉ ። በክፋትና በጭካኔ !

ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ በመንፈሳቸዉ ነጻ የሆኑ ሴት ናቸዉ። በሥጋ በማይመች ቦታ ታስረዋል። ግን በዚያ በማይመች ቦታ ሆነው የጣፈጠ እንቅልፍ ይተኛሉ። ዉስጣቸዉ በፍርሃት የተሞላ አይደለም። በራሳቸዉ ይተማመናሉ። ከማንም ጋር መኖር ይችላሉ። በየትም ቦታ ቢሄዱ ማንም አይነካቸዉ።አምስተኛ ልዩነት በሉልኝ!

እግዚአብሄር አቶ መለስን ከመነፈሳዊ እሥራት ወ/ት ብርቱካን ሚድቅሳ ደግሞ ከሥጋ እሥራት ይፍታቸዉ !

Friday, June 19, 2009

 

አቶ ስብሐት ነጋ በብርቱካን መታሰር ላይ

ሰኔ 12 ቀን 2001

የዘመኑ ቴክሎሎጂ ከፈጠራቸዉ የመገናኛና የመወያያ መድረኮች አንዱ ፓልቶክ ነዉ። በኢትዮጵያዉያን የሚንቀሳቀሱ በርጋታ ፓልቶክ ክፍሎች ከጊዜ ወደ ጊዜ እየበዙ ነዉ። ከነዚህ ፓልቶክ ክፍሎች መካከል የኢትዮ ሲቪሊቲ ፓልቶክ ክፍል አንዱ ነው። ይህ ክፍል ከሌሎች ክፍሎች የሚለየዉ ነገር ቢኖር 95 በመቶ አፍቃሪ ኢሕአዴጎችን ያሰባሰበ መሁኑ ነዉ። የክፍሉ አስተባባሪዎች ጠንካራ የገዢዉ ፓርቲ ደጋፊዎች ምናልባትም በሥርዓቱ ዉስጥ ትልቅ ቦታ ያላቸዉም ሊሆኑም ይችላሉ። በተለያዩ መጣጥፍት ለኢሕአዴግ አባላት፣ ፓርቲያቸዉ ከሕዝብ እንዲታረቅና ወደ ቀናዉ መንገድ እንዲመለስ ቀርቦላቸዋል። ከነርሱ ዉስጥ ጥሩ ልብ ያላቸዉ ሰዎች አይለዉ ወጥተዉ መልካም ነገር ሊፈጠር ይችላል የሚል ትንሽ ብትሆንና ከጊዜ ወደ ጊዜ እየመነመነች ብትመጣም ተስፋ ያለን ጥቂት አይደለንም።

በዚህ መንፈስ የኢሕአዴግ ደጋፊዎችን ለማነጋገር፣ ዉስጥ ዉስጡን ትልቅ ግፊት ማድረግ እንዳለባቸዉ ለማሳሰብ ወደዚህ የሲቪሊቲ አፍቃሪ ኢሕአዴግ ፓልቶክ ክፍል ገባሁ። በኔና በሚሊዮን በሚቆጠሩ ኢትዮጵያዉያን ዘንድ ትልቁና አንገብጋቢ ጉዳይ የሆነዉን በወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ ላይ እየተፈጸመ ያለዉን ኢሰብዓዊና ኢፍትሃዊ ግፍን በተመለከተ ሕሊና ያለዉ ሰዉ በሙሉ፣ ኢሕአዴግን እንደግፋለን የሚሉ ሳይቀር ድምጻቸዉን ማሰማት እንዳለባቸዉ አሳሰብኩኝ።
በክፍሉ ያሉ በርካታ የኢሕአዴግ ደጋፊዎች የወ/ት ብርቱካን መታሰር እንዳሳዘናቸዉና አጥብቀዉ እንደተቃወሙት፣ ለአመራር አባላቱም በግልጽ ያላቸዉን ትልቅ ተቃዉሞ እንዳቀረቡ ፣ ወደፊት ወ/ት ብርቱካን እንድትፈታ ጥረታቸዉ እንደሚቀጥሉ አሳወቁኝ። ምሳሌም እንዲሆን አቶ ስብሀት ነጋ በክፍሉ ቀርበዉ ቃለ መጠይቅ በተደረገላቸዉ ጊዜ በጣም ጠንካራ በሆነ መልኩ የወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ ጉዳይ እንደተነሳ ነገሩኝ። ቃለ መጠይቁን እንዳዳምጥ የኢንተርኔት አድራሻዉን አሳወቁኝ።

ጊዜም አልፈጀብኝም ከአቶ ስብሀት ነጋ ጋር የተደረገዉን ረጅም ቃለ መጠይቅ አዳመጥኩኝ። በቃለ መጠይቁ አብዛኛዉ በአሜሪካን ድምጻ ሬዲዪ አቶ ስብሀት ከተናገሩት ይልተለየ ነበር። ሕግ የበላይ መሆን እንዳለበት፣ ሐገ መንግስቱ መከበር እንዳለበት፣ ሕገ መንግስቱ እንደብርቅዬ ልንጠብቀዉ የሚገባ እንደሆነ አቶ ስብሀት አጠንክረዉ ተናገሩ። ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ በተመለከተ አባ መላ በሚል ስያሜ የሚታወቀዉ የክፍሉ ዋና አስተባባሪ የሚከተለዉን ጥያቄ አቀረበ። «አንዳንድ ጊዜ ከኢሕአዴግ በኩል፣ በዳያስፖራዉ የኢሕአዴግን ደጋፊዎች ሁሉ ሳይቀሩ፣ criticise የሚያደርጉት popular ያልሆኑ ነገሮችን ትወስዳላቹህ። አላስፈላጊ የሆነ። ለምሳሌ በቅርቡ በብርቱካን ሚደቅሳ ላይ የተወሰደዉ እርምጃ ምንም እንኳን ጥፋት አጥፍታለች ቢባልም ቴክኒካሊ፣ አስፈላጊ ያልሆነ confrontation ነዉ። ብዙ የምንሰራዉ፣ እንደ አገር የምንሰራዉ ብዙ ነገር አለ። በሕግ አንጻር ሁሉን ነገር እንደ ሌጦ መተርጎም የለብንም። ሌሎች moral values የሕዝብ አስተያየት የመሳሰሉ ነገሮችን ግምት ዉስጥ አስገብቶ ማየት ይገባል። የአንድ ጠንካራ መንግስት መለኪያዉ እርሱ ነዉ ብለን እናምናለን። ምን አልባት እነዚህን የመሳሰሉ ነገሮች፣ implication ያላቸዉን ጉዳዮች avoid ለማድረግ ኢሕአዴግ በኩል አንዳንድ ድክመት አለ። በሕዝብ ታዋቂ የሆኑ በጥሩም ሆነ በመጥፎ ተወዳጅነት ያላቸዉ የሙዚቃ ሰዉ ሊሆን ይችላል። ስፖርተኛ ሊሆን ይችላል። ወይም የፖለቲካ ሰዉ። በተለይ የብርቱካን ጉዳይ በኢትዮጵያ የፖለቲካ ታሪክ ዉስጥ እርስዎም እንደሚያወቁት፣ የሴቶች ታጋዮች ሚና በጣም በጣም ትንሽ ነዉ። በተቃዋሚም እንኳን ብትሆን «በሕጋዊና በሰላማዊ መንገድ እታገላለሁ» ብላ የገባች እስከሆነች ድረስ፣ በአምጽ የሚታገሉትን ተቃዉመን፣ ጠመንጃ ከሻቢያ ጋር አንስተዉ ግለሰቦችን ለመግደል፣ ተቋሞችን ለማፍረስ፣ የሚንቀሳቀሱትንም እያወገዝን፣ በሰላም «አገሬ ዉስጥ ሕግና ሕገ መንግስት አለ። መንግስትን ፊት ለፊት እታገላለሁ» ብሎ የገባዉንም ኃይል እኩል treat ማድረግ የለብንም። በተለይ ሴት በመሆኗ፣ የልጅ እናትም በመሆኗ በኢትዮጵያ ዉስጥ የሴቶችን ሚና ከፍ ለማድረግ ከፍተኛ እምነት አለዉ ብዬ ስለማምን፣ ኢሕአዴግ በእንደዚህ አይነት ሰዎች ላይ የምትወስዱት እርምጃ በምንም መልክ defend ልናደርግ justify ልናደርግ እያቃተን ነዉ። ከእንደዚህ አይነት unpopular ድርጊት መቼ ነዉ ኢሕአዴግ የሚገደበዉ? ይሄን ጉዳይ በቅርቡ ለመፍታት የታሰበ ነገር አለ ወይ ?»

እዚህ ላይ አባ መላ ለመናገር እንደሞከረዉ ገዢዉ ፓርቲ በወ/ት ብርቱካን ላይ የወሰደዉ እርምጃ በምንም መልኩ ሚዛን የማይደፋ፣ የራሳቸዉን ደጋፊዎች እንኳን ማሳመን ያልቻለ ትልቅ ስህተት እንደሆነ እናያለን።

በመርህ ደረጃ ማንም ሰዉ ለሕግ መገዛት እንዳለበትና ከሕግ በላይ ሊሆን እንደማይችል አቶ ስብሃት ከተናገሩ በኋላ የሚከተለዉን ነበር ያሉት፡

«ማንኛዉ እርምጃ ሲወሰድ በጥልቀት የማንኛዉም እርምጃ መነሻዉና መድረሻው ጠቃሚነቱና ጉዳቱ መታወቅ አለበት። ማንኛዉም እርምጃ ጉዳት የሌለዉ የለም። እኔ ወደ ቤቴ ከዚህ ስሄድ risk አለዉ። ግን አልሄድም ልል አልችልም። መሄድ አለብኝ። ስለዚህ risk የሌለዉ ነገር የለም።ጉዳቱን ጥቅሙ የትኛዉ ይበለጣል ነዉ። ብርቱክንን ማሰር ጉዳት አለዉ። ጥቅሙስ ? ጉዳቱና ጥቁምን ማስረዳት አለመቻላችን፣ አለማስተማራችን፣ አለማሳወቃችን፣ ከመደረጉ በፊትም ከተደረገም በኋላም ጉድለታችን ይመስለኛል። ከዚህ ባሻገር «አሁን ምን እየታሰበ ነዉ» ላልለከዉ እኔ በአገር ጥቅም ላይ compromise እርቅ መምጣት የለበትም። ማንኛዉም ሰዉ ከጥፋቱ በላይ መቀጣት የለበትም። ከጥፋቱ በታችም መቀጣት የለበትም። የፈጸመዉን ቅጣት የሚመጥን ቅጣት ማግኘት አለበት። ስለዚህ ብርቱክናም የፈጸመችዉን ጉዳት የሚመጥን ቅጣት ማግኘት አለባት። ከዚያ በታች ሳይሆን ከዚያ በላይ ሳይሆን። ምንድን ነዉ ጥፍቷ ? ከሰላም ጋር የተያያዘ ነዉ ? ምንድን ነዉ የተከሰሰችበት አንቀጽ ? አላዉቀዉም ! አንቀጹ ምን ያስቀጣል ? አላዉቀዉም። ግን ፍትሃዊና ቀልጣፋ ፍርድ ግን እንድታገኝ እመኝላታለሁ።»

እዚህ ላይ አቶ ስብሀት «ብርቱካን የተከሰሰችበትን ጥፋት አላዉቀዉም» ነዉ የሚሉን። አቶ ስብሀት ብርቱካን ለምን እንደታሰረች ያጡታል ብዬ አላምንም። ነገር ግን ወ/ት ብርቱካን ላይ የደረሰዉ ግፍ አተፋች የተባለዉን በጭራሽ የሚመጥን እንዳልሆነ፣ አተፋች የተባለዉም በሕግ ፊት ሚዛን የሚደፋ እንዳልሆነ የተረዱና የሚያምኑ ይመስለኛል። በዚህም ምክንያት እንደ ኢሕአዴግ ከፍተኛ አመራር አባል እነ በረከት የሚመልሱትን መልስ ለመመለስ የከበዳቸዉና እንዲሁ በደፈናዉ «አላዉቅም» ብለዉ ማለፉን የመረጡ ይመስላል።

ከአንዳንድ ምንጮች ለመረዳት እንደተቻለዉ በኢሕአዴግ ዉስጥ በጣም አክራሪና ግትር ከሚባሉት መካከል አቶ ስብሀት ነጋ አንዱ ናቸዉ። እኝህ ሰዉ ከሁለት አመታት በፊት የቅንጅት መሪዎች መፈታት የለባቸዉ የሚል ጠንክራ አቋም የነበራቸዉ ሲሆን ለረጅም ዘመን የድርጅቱ መሪ እንደመሆናቸዉ ከበስተጀርባ ሆነዉ እንደ ቀድሞ የጣሊያን ማፊያ መሪዎች ብዙ ነገሮችን የሚያሽከረክሩ ናቸዉ የሚሉ ጥቂቶች አይደሉም። ከዚህ በፊት ባደረጉት ቃለ መጠይቅ «ቅንጅት ጠላት ነዉ» የሚል አሳፋሪና አሳዝኝ አባባል መጠቀማቸዉም ይታወሳል።

ኦዲዮዉንም ለማዳመጥ ከታች ያለዉ የኢንተርኔት አድራሻ ጋር ይሂዱ !

http://peacewithkinijit.tripod.com/sibhat.wma

Wednesday, June 17, 2009

 

በቃሊቲ እሥር ቤት ሰሞኑን የተከሰተዉን አሳዝኝ ሁኔታ በተመለከተ - ግርማ ካሳ

ሰኔ 9 ቀን 2001

ቶርቸር (ሰቆቃ) ከአለም እንዲጠፋ የሚታገል የአለም አቀፍ የጸረ-ቶርቸርና የተጎጂዎች ደጋፊ ድርጅት፣ የአይምሮን ቶርቸር ሲተነትን፣ ረዘም ላለ ጊዜ በጨለማ ቤት ዉስጥ ማስቀመጥን፣ እንቅልፍ ማሳጣትን፣ መድፈርንና የመሳሰሉትን ከቶርቸር ዉስጥ ያስገባቸዋል። በእንደዚህ አይነት የአይምሮ ቶርቸር የሚያልፉ ሰዎች እራሳቸዉን እንዲጠሉ የሚያደርግና የሚቆይ ከፍተኛ የአይምሮ በሽታን እንደሚያመጣ ይናገራሉ።[1]

የለንደን ዪኒቨርሲቲ ተመራማሪዎች ከቤልግሬድ የሕክምና ኮለጅ ጋር በመተባበር 279 የቀድሞ እሥረኞችን በማነጋገር፣ ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ መረጃዎችን ሰብስበዋል። በሰበሰቡትም መረጃ መሰረት የደረሱበት ድምዳሜ የአይምሮ ቶርቸር ከአካላዊ ቶርቸር በምንም እንደማይለይ የሚገልጽ ነበር። የአይምሮ ቶርቸርን እንደ አካላዊ ቶርቸር የሚያግድ አለማቀፋዊ ሕግ መዉጣት እንዳለበትም አሳስበዋል።[2]

እሲት ለትንሽ ጊዜ ከምናደርጋቸዉ እንቅስቃሴዎች ቆጠብ እንበል። አይኖቻችንን እንጨፍን። እራሳችንን ሁለት ሜትር በሁለት ሜትር ባለች ጠባብ ክፍል ዉስጥ እንየዉ። የምንተኛበት መኝታ በጣም ይቆረቁራል። ከመጨለሙ የተነሳ ብዙም አይታየንም። ከእንቅልፋችን ስንነሳ ጨለማ ነዉ። ወደ መኝታ ስንሄድ ጨለማ ነዉ። በቀዳዳ፣ ሕይወታችንን ለጊዜው የሚያቆይ አፍ ላይ የሚደረግ ይወረወርልናል። ተኝተንም ሳለ የወፎችን ጫጫታ ወይንም ሙዚቃ ወይንም የሰዎች ድምጽ ሳይሆን የአይጦችን ጭጭጭ የሚል ድምጽ ነዉ የምንሰማዉ። አንዳንዴም አይጦቹ በተኛንበት በላይችን ላይ ይበራሉ። መጽሃፍ ማንበብ አንችልም። ሬዲዮ መስማት አንችልም። ቴሌቭዥኑንማ እርሱት።

መልካችንን የምናይበት መስታወት የለም። መስታወትም ቢኖር ጨለማዉ መስታወቱን ተራ ግድግዳ አድርጎታል። ቢገድሉን ወይንም ቢደበድቡን ደስ ይላቸዉ ነበር። ግን የምእራቡን አለም ይፈራሉ። ስለዚህም በቀላቸዉን በሌላ ነገር ይወጡታል። አዉቀዉ ትናንሽ ጉንዳንና ቱሃን ይለቁብናል። ጉንዳኖቹና ቱሃኖቹ ሰዉነታችንን ይነክሳሉ። አንዱን ከእጃችን ስናራግፍ አንዱ በእግራችን ይመጣል።ሰዉነታችን ይላላጣል። «የሐኪም ያለህ» ብንል የሚሰማ የለም። ብናለቅስ የሚሰማ የለም። ግድግዳዉን ብንደበድብ የሚሰማ የለም። ብንለምን ፣ «እባካችህ በእመብርሃን ፣ በመድሃኔ አለም፣ በጊዮርጊስ ፣ በአላህ» ብንል የሚሰማ የለም።

ለአንድ ቀን ብቻ አይደለም። ከአንድ ቀን አልፎ ለሁለት ቀናት …. ከዚያም ለሶስት ቀናት ..ለአሥር ቀናት …. ለሃያ ቀናት …. ቀኑ እየተራዘመ መጣ። ቀናት መቁጠራችንን ቀጠልን። አንድ መቶ ስድሳት አምስት ላይ ደረስን። እሲቲ እናስብ እራሳችንን ! አናብድም ? አይምሯችንን አንስተም? እራሳችንን አንጠላም? አንታመም ?

በወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ ላይ የደረሰዉ እንግዲህ ይሄ ነዉ። በእጇ ጠመንጃ አልያዘችም። ሁለንም የምትወድ ናት። ፍቅርን ፍትህን አንድነት ነዉ የሰበከችዉ። በምቾት ተሰዳ በምእራቡ አለም መኖር ስትችል አገሬንና ህዝቤን ብላ ለአገሯ ለመታገል የወሰነች አገር ወዳድ ሴት ናት።

ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ ከታህሳስ 20 2001 ዓ.ም ጀመሮ እስከ ሰኔ 7 ቀን 2001 ድረስ በግፍና በጭካኔ በጠባብ ጨለማ ክፍል ዉስጥ፣ ከሰዉ እንዳትገናኝ ተደርጎ ከጉንዳንና ከአይጦች ጋር ነዉ የምትወለዉና የምታደረዉ። ፍርድ ቤት ትእዛዝ ቢሰጥም ከዘመድ ወዳጅ፣ ከሃኪም ከጠበቃዋ ጋር እንዳትገናኝ ታግዳለች።

ማክሰኞ ሰኔ 4 2001 ዓ.ም ትልቅ አስደንጋጫ ክስተት ተፈጠረ። የስድስት ወር ቶርቸር የወለደዉ እጅግ በጣም አሳሳቢ ነገር ነበር።በርጋታዋና በብርታቷ የምትታወቀዉ ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ ከታሰረችበት አካባቢ ከፍተኛ ጩኸት እንደተሰማ አቡጊዳ ዘገበ። ለምን ወ/ት ብርቱካን እንደጮኸች እስከአሁን ማወቅ አልተቻለም። ከሰዉ እንዳትገናኝ አድርገዉ ምን እያደረጓት እንደሆነ እግዚአብሄር ነዉ የሚያወቀዉ። [3]

የመጀመሪያዉ አላማቸዉ ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ እንድትል የሚፈልጉትን ብላ የፖለቲካ ተቀባይነት እንድታጣ ለማድረግና ትግሉን መሪ አልባ ለማሰኘት ነበር። አስፈራሯት። ዛቱባት። እርሷ ግን ናቀቻቸዉ። ለነርሱ ዉሸት እንደማትንበረከክ አሳየቻቸዉ።

እነርሱም በእልህና በጭካኔ መጡባት። «እንግዲያወስ በፈቃዷ ለኛ ፈቃድ ካልተገዛች፣ ቶርቸር አድርገን መንፈሷን ሰባብረን ዋጋ ቢስ እናደርጋታለን! እናሳብዳታለን !» ብለዉ ተነሱ። ብዙ ነፍሳት በገደለ ነፍሰ ገዳይ እንኳን ያልተፈጸመ በደል አደረሱባት። ለስደት ወር በጨለማ ቤት ዉስጥ በግፍ አስቀመጧት።

አቡጊዳ እንደዘገበዉ የማረሚያ ቤቱ ሃላፊዎች በማንም ሰዉ ላይ እንደዚያ ተደርጎ እንደማያዉቅ፣ በወ/ት ብርቱካን ላይ የሚደረገዉ ግፍ ከላይ በመመሪያና በትእዛዝ የመጣ እንደሆነ ይናገራሉ። (ከአራት ኪሎ ማለት ነዉ)

ለመሆኑ አራት ኪሎ የተቀመጡት ሰዎች (ሰዎች ልበላቸዉና) ይሄ ሁሉ ግፍ በዚች ሴት ላይ እንዲደርስ የሚፈቅዱት ምን ወንጀሏ ብትሰራ ነዉ ? «ወያኔ ጠላት አይደለም» ማለቷ ነዉ ወንጀሏ? ሰላማዊና ሕጋዊ ትግል ማድረጓ ነዉ ወንጀሏ? አገሯን ለቃ በስደት አለመኖሯ ነዉ ወንጀሏ?

«ለሕግ የቆምን ነን። ሕግ መከበር አለበት» ይሉናል። የትኛዉ ሕግ ? ሕግን ቢያወቁ ኖሮማ የፍርድ ቤትን ዉሳኔ ባከበሩ ነበር ? ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ በጠበቃዎቻቸዉና በሃኪሞቻቸዉ በወዳጆቻቸዉ እንዲጎበኙም በፈቀዱ ነበር። ይቅርታዉን ከመሰረዛቸዉ በፊትም ሕጉ እንደሚያዘዉ፣ በጽሁፍ ምክንያታቸዉን ያሳዉቁና ለወ/ት ብርቱካንም፣ ምላሽ እንድትሰጥ፣ የሃያ ቀናት ጊዜ ይሰጡ ነበር።

የሕወሃቱ መሪ አቶ መለስ ዜናዊ ለቢቢሲዉ ሃርቶክ ጋዜጠኛ ስለወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ ተጠይቀዉ ሲመልሱ “ከተፈታች በኋላ ይቅርታ አልጠየኩም አለች። ያ ማለት ይቅርታ ያገኘቸዉ በማጭበርበር ነበር ማለት ነዉ። ስለዚህ በሕጋችን መሰረት በማጭበርበር የተገኘ ይቅርታ ወዲያዉኑ መሰረዝ አለበት” ነበር ያሉት።

“የይቅርታ ዉሳኔ ለይቅር ተባዩ ከደረሰና ተቀባይነት ካገኘ በኋላ የይቅርታ ዉሳኔ በማጭበርበር ወይም በማታለል የተገኘ መሆኑ ከተረጋገጠ የይቅርታ ዉሳኔዉ ዋጋ አይኖረዉም”[4] የሚለዉን በይቅርታ ስነ-ስርዓት አዋጅ ቁጥር 395፣ አንቀጽ 16፣ ንኡስ አንቀጽ 2 አስበዉ ይመስለኛል አቶ መለስ ይህ አይነት መልስ የሰጡት።

አዲስ አድማስ በሚባለዉ አገር ዉስጥ በሚታተም ጋዜጣ በይፋ በወጣዉ ጽሁፏ፣ ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ ስትጽፍ “ በሽማግሌዎቹም የእርቅ ማግባቢያ መንፈስ መሰረት በፖለቲካ የተቀሰቀሰዉን ክስ ፖለቲካዊ እልባት ለመስጠት በማሰብ ለእርቅ ስል ከሌሎች የፓርቲዉ መሪዎች ጋር ተስማምቼ ሰኔ 11 ቀን 1999 ዓ.ም በተጻፈዉ ሰነድ በሽማግሌዎች አማካኝነት ይቅርታ ጠይቂያለሁ። ይህ ብፈልግም ልለዉጠዉ የማልችለዉ ሐቅ ነዉ» ነበር ያለችዉ።[5]

እንግዲህ እዚህ ላይ የምናየዉ ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ በግልጽ «ይቅርታ ጠይቂያለሁ» እንዳለች ነዉ። ታዲያ አቶ መለስ ዜናዊ ከየት አምጥተዉ ነዉ «ይቅርታ አልጠየኩም አለች» እያሉ የሚናገሩት? የቱ ላይ ነዉ ወ/ት ብርቱካን ያጭበረበረችዉ ? ምንድን ነዉ ያታለለችዉ ? ምኑ ነዉ ጥፋቷ እንደዚህ ኢሰብአዊና አረመኒያዊ ግፍ ድርጅታቸዉ በዚች ሴት ላይ የሚያወርድበት ?

ዋሺንግተን ፖስት እንደዘገበዉ ወይዘሪት ብርቱካንን ጨምሮ የቅንጅት መሪዎች፣ የሰብዓዊ መብት ተከራካሪዎችና ጋዜጠኞች በአገር ሽምግልና መሰረት ይቅርታ ጠይቀዉ በተፈቱ ጊዜ አቶ መለስ ዜናዊ የተናገሩት አባባል ነበር። «ይቅርታዉ ሙሉ ነዉ። ሕግን እስካከበሩ ድረስ ለመምረጥና ለመመረጥ ይችላሉ። ያለፈዉን ትተን፣ ወደኋላ ሳንመለስ ወደፊት ነዉ ማየት ያለብን» [6]ነበር ያሉት። ታዲያ «ወደ ኋላ አንመለስ። ያለፈዉን እንተዉ» ብለዉን እራሳቸዉ ግን ወደ ኋላ ተመልሰዉ «ይቅርታ ጠይቂያለሁ» ያለችዉን ሴት «ይቅርታ አልጠየኩም ብላለች» ብለዉ እንደነፍሰ ገዳይ ድርጅታቸዉ ማሰቃየቱ ምን ይባላል ? «

«ሕግን እስካከበሩ ድረስ» ድረስ ነበር ያሉት አቶ መለስ ዜናዊ። ታዲያ ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ የትኛዉን ሕግ ነዉ የጣሰችዉ ? ጠመንጃ አንስታ ሰዉ ገደለች? ወይንም የሕዝብን ገንዘብ መዝብራ ገንዝብ ወደ ዉጭ አሸሸች? ወይስ ጉቦ ተቀብላ ባገኘችዉና ባጠራቀመችዉ ገንዘብ አሜሪካ አገር ቤት ሰራች ? የቱ ነዉ ወንጀሏ ለዚህ ሁሉ ግፍ የዳረጋት ?

እንግዲህ አገር ፍረድ ! አሁን ያለዉን አገዛዝ እንደግፋለን የምትሉ፣ ልብና አይምሮ ያላቹህ ሁሉ ፍረዱ ! እንስሳዉና አዉሬዉስ እንስሳና አወሬ ነዉ። «ሰዉ ነን። እናስባለን፣ እናገናዝባለን» የምትሉ ሁሉ ፍረዱ ! የዚች ሴት ጥፋት ምንድን ነዉ ? እንደዚህ ቶርቸር የምትደረግበት ምክንያቱ ምንድን ነዉ ?

ይሄን ያህል ጭካኔ በሌላ ወገናችን ላይ እስክናደርስ ድርስ እንደዚህ አዉሬ የሚያደርገንስ ነገር ምንድን ነው ? ምን ይሻለን ይሆን ባካችሁ ? ለምንድን ነዉ እንዲህ የምንጨካከነዉ ? ለምንድን ነዉ አንዱ ሲጠቃ ሌላዉ ዝም ብሎ የሚመለከተዉ? ለምንድን ነዉ አንዱ ደብድብ ሲል ሌላዉ እሺ ብሎ የሚታዘዘዉ ? ምንድን ነዉ እንደዚህ ሕሊና ቢሶች ያደረገን ?

ኧረ አንተ ደጉ መድሃኔአለም ኢየሱስ ክርስቶስ በቃቹህ በለን ! እባክህን እኛም እንደሌሎቹ ሕዝቦች እንደታደሉት፣ ለተጠቁት የምንቆም፣ ለድሃ አደጉና ለመበለቲቶች የምንሟገት፣ የወደቀዉን የምናነሳ፣ የተሰበረዉን የምንጠግን፣ ክፋትንና ጭካኔ ቶርቸርን የምንጸየፍና የምንቃወም እዉነተኞች አድርገን !!! ብርቱካን ሚደቅሳንም አስባት ! ባላችበት ቦታ ኃይልህና ብርታትህ ጸጋህና ጥበቃህ አይለያት!





[1] http://www.tassc.org/index.php?sn=78
[2] http://www.abc.net.au/science/news/stories/2007/1864094.htm
[3] http://www.abugidainfo.com/?p=9813
[4] http://www.fsc.gov.et/Negarit%20Gazeta/Gazeta-1996/Proc%20No.%20395-2004%20Procedure%20of%20Pardon.pdf
[5] http://n.b5z.net/i/u/6142638/i/birtukan_1_.pdf
[6] http://www.washingtonpost.com/wp-dyn/content/article/2007/07/20/AR2007072000454.html

Thursday, June 11, 2009

 

THE TWO WOMEN THAT ARE SHAKING TYRANTS


Girma Kassa
(muziky68@yahoo.com)

June 11, 2009

Both are at same ages. Both had noble professions. Both are courageous. Both are not afraid to tell the truth. Both are standing against a regime that is tyrannical, deceptive and hateful. Both are women. Both represent, in their own way, the best of this new generation. Both have a baby child. Both lived at the same place at one time, kaliti prison.

I am talking about Birtukan Mideksa and Serkalem Fassil. I would like to use this opportunity to salute these two sisters of ours, for their courage and for what they have done for the cause of freedom and well-being of Ethiopia.

Birtukan Mideksa was arrested four years ago, on phony charges, and sentenced to life imprisonment in the notorious, full of big rats Kaliti prison. At that time Birtukan Mideksa's daughter Hale was a 7 months old baby.

Serkalem Fassil , jailed at the same prison with Birtukan Mideksa, was pregnant. Recalling her pain in Kaliti prison, and in her letter she send to Global Forum of Freedom Expression forum, Serkalem characterized the regime as immoral. "As my pregnancy progresses, I slept many sleepless and tearful nights. Prison officials were so sadistically content with my pain. The sleeping arrangement was my longest nightmare of the prison experience. It symbolizes the moral bankruptcy of the Tyrants. It was tantamount to a long and deliberate torture." she wrote.

Birtukan Mideksa is arrested for a second time and placed in solitary confinement for more than hundred and sixty three days now, a punishment even rapists and serial killers have not had. Her apparent crime, as Newsweek Tepperman explained it, is to "organizing a democratic challenge to the increasingly iron-fisted rule of Prime Minister Meles Zenawi.".

Serkalem Fassil has been denied - for the third time - a visa to travel to Europe and attend the Global Forum of Freedom Expression. She was denied to publish a newspaper and exercise her constitutional right.

On December 28th 2008, 10 armed soldiers jumped out from their four heavily armed vehicles to detain just one woman, Birtukan Mideksa. When Serkalem Fassil was sent at the police hospital to deliver her baby, four heavily armed strong soldiers were guarding her. Ten strong men for one woman and four strong men for another!!!!!

By arresting Birtukan Mideksa, the regime has made itself more isolated. More and more of its officials are embarrassed on the international scene and Birtukan Mideksa is gaining national and international status. She is mobilizing people from within her cell. She has become the symbol of resistance and justice. She is winning by loosing.

By denying exit VISA to Serkalem Fassil, the regime again has exposed itself. It has shown that it is weak, lacking confidence, immoral and in deep trouble. In the Global Forum of Freedom Expression annual meeting, the chair assigned to Serkalem Fassil was empty. However her name was displayed in big. The Empty chair has sent a very powerful message, perhaps even more if Serkalem would have attended physically the meeting.

By arresting Birtukan Mideksa and denying constitutional rights of Serkalem Fassil, the regime has benefited nothing. To the contrary it is damaging itself internationally and showed to the world its barbarism, brutalities and IMMORALITIES.

Ethiopia is lucky to have braves like Birtukan Mideksa and Serkalem Fassil, women of actions, who love their country and are visionaries. " Because we have seen twenty three African countries conform into democracies, we know Ethiopia can there" said Serkalem Fassil believing in the power of the people.

"The Sun has risen to Ethiopia. Darkness is no more." said Birtukan Mideksa. "Where is the sun, where is the light ?" some may ask. However, Birtukan have seen the light because she put on new glasses on her eyes, that helped her see the strong desire, and thirst of democracy that is actively burning within the mind and heart of millions of Ethiopians.

Agents of darkness have been trying to extinguish the emerging light. They have been desperately going over the edges to preserve the status quo and make sure we stay in darkness. Their evil actions against Serkalem and Birtukan are parts of these activities. However, they are failing. The END of agents of darkness has begun. With a little nudge from the people, the era of dictatorship and tyranny will be over.

It is therefore time for the rest of us, who have been basically silent, to come out from our closets and join the struggle for real and create the little nudge that is necessary to bring visible results. This is not a game; this is a serious matter that concerns the destiny of 80 millions people.

As Carmen de Monteflores said " Oppression can only survive through silence". Therefore should we continue to give only leap services in view of the suffering of our country, should we fail to seriously contribute our share to the struggle of democracy and justice , Should we be selfish and engaged only in personal matters, we can consider ourselves as dead people. "Our lives begin to end the day we become silent about things that matter" said Dr Martin Luther King. We determine our destiny, not few groupies.

Birtukan Mideksa and Serkalem Fassil, without firing bullets have been able to shake up the regime in their own way. Had we all become more like them, our country would not have been where it is now. If we follow the footsteps of these women, if we start believing in ourselves, if we do not allow ourselves taken away by the talk of despair and hopelessness, if we stop saying “It is impossible” and allow ourselves to be filled with ‘the I can do attitude”, we will surely prevail. black Americans did it. South Africans did it. Indians did. Why shouldn't we do it as well ! Are we not human beings like them ?

As Serkalem Fassil said “ Ethiopia shall be free from Tyranny”. Behold, in front of us the new era and the new beginning ! Let us all stand up and march towards the noisy Jordan River and cross it. Let us inherit the promise land !



 

«ብርቱካንን እወዳታለሁ»

በወርቀ አማኑዕል ዘሰላም
(muziky68@yahoo.com)

ሰኔ 4 ቀን 2001 ዓ.ም

አሜሪካን አገር ተሰድጄ ከወጣሁኝ በርካታ አመት አለፈኝ። አዲስ አበባ የነበርኩኝ ጊዜ የግል ትምህርት ቤት ስለተማርኩኝ እንግሊዘኛ ብዙ አይችግረኝም። ከፈረንጆች ጋር በኢትዮጵያዊ አክሰንቴ ደህና እግባባለሁ። ነገር ግን እንደ አማርኛ የዉስጤን የሃሳቤን መናገር አልችልም።

አንድ ቀን አብሮኝ የሚሰራ የሕንድ ተወላጅ ጓደኛዬ ቤቱ ጋብዞኝ እሄዳለሁ። በዚያ ከሁለት ልጆቹ አንዷ፣ ኮሌጅ ልትገባ አንድ አመት የቀራት፣ በጉጅራቲ(በሕንድ ከሚነገር ቋንቋዎች አንዱ) አባቷን ስታናግር ሰማሁኝ። ልጅቷ በቅርብ ከሕንድ የመታጭ መሰለኝ። ነገር ግን ልጆቹ አሜሪካ አገር እንደተወለዱ ጓደኛዬ ሲነግረኝ ተገረምኩኝ። ለምን ? የማዉቃቸዉ ብዙ ኢትዮጵያዉያን ልጆቻቸዉ አማርኛ የማይናገሩ በመሆናቸዉ !

ይህ ሕንድ እንዴት ልጆቹን በአገሩ ቋንቋ እንዳስተማረ ጠየኩት። «ሙሉ ለሙሉ የወላጆች ጉዳይ ነዉ። ወላጆች ልጆቻቸዉን በሚፈልጉበት መሥምር በልጅነታቸዉ መምራት ካልቻሉ ጥፋቱ ልጆቹ ላይ ሳይሆን ወላጆቹ ላይ ነዉ።” አለኝ። እኔም ያን ጊዜ፣ የኔ ልጆች አማርኛ የሚያወቁ ይሆናሉ ብዬ በዉስጤ ዛትኩኝ።

ጥቂት አመታት አለፉ። ጊዜ መድረሱ አይቀርም፣ እዚሁ አሜሪካን አገር የተዋወኳትን አንዲት የአገሬን ልጅ አግብቼ እናቷን የምትመስል ቆንጅዬ ሴት ልጅ ወለድኩኝ። ከባለቤቴ ጋር ተመካክረን የአማርኛዉን ጉዳይ ከልጃችን ጤንነት ቀጥሎ ትልቅ ቦታ ሰጠነዉ። ይኸዉ አሁን አሥራ ሁለት አመቷ ነዉ፤ ቀልጣፋ የአማርኛ ተናጋሪ ወጥቷታል። ወላጆቻችን ከኢትዮጵያ እኛን ለመጠይቅ ሲመጡ እንደሌሎች የአበሻ ልጆች የኔ ልጅ ተርጓሚ አላስፈለጋትም። ኢትዮጵያ ለጉብኘት ስትሄድም እንደልቧ እያወራች ተቀላቅላና ተሳስቃ ትመለሳለች።

ከአራት ወራት በፊት አንድ ነገር ሆነ። ስልክ ይዤ አወራለሁ። ልጄ ትንሽ ራቅ ብላ ታዳምጣለች። ያናደደኝ፣ ያሳሳዘኝ ነገር እንዳለ አወቀች። ስልኬን ጨርሼ ወደ ሶፋዉ ሄድኩኝና ተቀመጥኩ። እንደመተከዝ ብሎኛል። የምትሰራዉን ትታ ከጎኔ ተቀመጠች። «ምን ሆነሃል ባባ ?» አለችኝ። «ዳዲ» የሚለዉን ስለምጠላዉ «ባባ» ነዉ ልጄ የምትለኝ። (ፈረንጆች ልጆቻቸዉ ዳዲ ይበሏቸዉ ከፈለጉ) «ደህና ነኝ። ምን አልሆንኩኝም » አልኩኝ ያበሳጨኝንና ያሳዘነኝን ለመሸፋፈን ፈልጌ።

ዝም ብላ ለጥቂት ደቂቃ ደረቴ ላይ ከተኛች በኋላ «ብርቱካን ማን ናት ?» አለችኝ። ወዲያው «ክዉ አልኩኝ» ። በስልክ ሳወራ የነበረዉ በወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ ላይ የደረሰዉን ግፍ በተመለከተና እንዴት አሳዛኝና አሳፋሪ ድርጊት ወያኔ-ኢሓዴግ እንደፈጸመ ነበር። የምመልሰዉ ግራ ገባኝ። ምን እንደምላት አሰላሰልኩና «አንድ ታዋቂ ሴት ናት» የሚል መልስ ሰጠሁ። «ኢትዮጵያ ነዉ የምትኖረዉ? ምን ሆነች ባባ » አለችኝ። «አዎ ኢትዮጵያ ነዉ ያላቸዉ። ታስራለች» አልኩኝ። ጥያቄዉ አላቆመም። «ለምን ታሰረች ? » የሚል ጥያቄ ቀረበ። ቁና ቁና መተንፈስ ጀመርኩኝ። ኢትዮጵያን እንዳትጠላብኝ በኢትዮጵያ የሚደረገዉን ግፍ ልነግራት አልፈለኩ ነበር። እርሷ ግን ለምን እንደሆነ አላወቅም አጥብቃ ጠየቀች።

«ምንም ነገር ሳታጠፋ ነው የታሰረችዉ» አልኳት። «እንዴ ባባ ? ጀጅ የለም እንዴ ? » አለች። «ጀጅ አይደለም ዳኛ ነዉ በአማርኛ የሚባለዉ» ብዬ እርማት ሰጠሁና «ዳኛ አለ። ግን እዚያ ያለዉ መንግስት ጥሩ መንግስት አይደለም። ዝም ብሎ ሰዉ ያስራል። ሰዉ ይገድላል። ሕግ አያከብርም።» አልኳት። ለዚህ ነዉ እናንተ አሜሪካን አገር የመጣችሁት ? አለችኝ። «አዎን ? » ብዬ መለስኩ። «ኢትዮጵያን ጠለኋት ባባ» አለችኝ። ወዲያዉ ዉስጤ ደንግጦ «ይሄማ አይሆንም። ኢትዮጵያ ማለት እኮ እኔ፣ እናትሽ፣ አክስቶሽ፣ አጎቶችሽ ..ማለት ነዉ። ኢትዮጵያን መጥላት ማለት እኛን መጥላት ማለት ነዉ። አንቺን እራስሽንም መጥላት ነዉ።» ብዬ የአሜሪካንን ታሪክ በማንሳት ለማስረዳት ሙከራ ጀመርኩኝ።

አሜሪካን አገር ስለነበረዉ የሲቪል ራይት እንቅስቃሴ በተለይም ስለ ዶር ማርቲን ሉተር ኪንግና ሮዛ ፓርክ ፕሮጀክት ነገር በትምህርት ቤቷ ሰርታ ነበር። ያንን አስታወስኳት። በአሜሪካ የነበረዉን ችግር ፣ እንዴት ጥቁሮች እንደተበደሉ ገለጽኩላት። አሜሪካ መጥፎ ሰዎች ቢኖሩም ጥሩ ሰዎች ብዙ ስለደከሙ አገሪቷን ቀየሯት። ኢትዮጵያንም በተመለከተ ኢትዮጵያን መጥላት ሳይሆን መፍትሄዉ እንደ አሜሪካ ኢትዮጵያን መቀየር ነዉ። እነብርቱካን ልክ ያኔ እነ ማርቲን ሉተር ኪንግና ሮዛ ፓርክ እያደረጉት እንደነበረዉ እያደረጉ ነዉ። ያኔ ማርቲን ሉተር ኪንግ ሳያጠፋ እንደታሰረዉ ነዉ አሁንም ብርቱካን ሳታጠፋ ነዉ የታሰረቸዉ።» አልኳት።

«አንተ ታዉቃታለህ ? » አለችኝ። «አዎ አውቃታለሁ» አልኳት”። «እኔንስ ታወቀኛለች» አለች። «አንቺን አታወቅሽም። ግን ለአንቺና ለሌሎች ልጆች ወደፊት ጥሩ አገር እንዲኖራቹህ ለማድረግ ስትል ነዉ የታሰረቸዉ» አልኳት። «ልጅ አላት» አለችን። «አዎ የአራት አመት ሴት ልጅ አላት።» አልኳት። ያኔ ልጄ ማልቀስ ጀመረች።

ከሁለት ቀናት በኋላ ኮምፒተሬ ላይ ቁጭ ብዬ ስሰራ አሁንም እንደልማዷ እግሮቼ ላይ ቁጭ አለች። «ባባ የብርቱካንን ፎቶ ታሳየኛለህ? » አለችኝ። ወዲያዉ ወደ ድህረ ገጾች ሄጄ አሳየኋት። «ባባ እኔ ብርቱካንን እወዳታለሁ !» አለችኝ። «አንቺ ብቻ አይደለሽም። በኢትዮጵያ ዉስጥ ሕዝብ ሁሉ ነዉ የሚወዳት። አይዞሽ ትፈታለች። እግዚአብሄር ከርሷ ጋር ነዉ። እግዚአብሄር ካለ ደግሞ በአይንሽ ታያታለሽ። ሁልጊዜ ማታ ማታ ግን ከመተኛትሽ በፊት ጸልይላት» አልኳትና ግንባሯን ስሜ አሰናበትኳት።

«አይዞሽ ትፈታለች!» ያልኩት በአይምሮዬ ሕይወት እንዳለዉ እንደሚራመድ ነገር መንቀሳቀስ ጀመረ። ትላንት «ትፈታለች» በማለት አንድ፣ ሁለት እያልን ነበር የምንቆጥረዉ። አሁን አንድ መቶ ስድሳ ስምንት ደርሰናል። «መቼ ነዉ የምትፈታዉ? እንዴት ነዉ የምትፈታዉ ? » የሚሉት ጥያቄዎች በአይምሮዬ ይመላለሱ ጀምር።

በዉስጤ ለጥቂት ደቂቃዎች ብዙ ሃሳቦች ከተጋጩ በኋላ ሁሉም ወደ አንድ መሥመር መጡልኝ። የጠራ ሁኔታ ይታየኝ ጀመር። አሁን ያለዉን አገዛዝ የፖለቲካ ክስረት አየሁ። ብርቱካን ሚደቅሳ እሥር ቤት ሆና የታጠቁ ኃይላት ተጨፍልቀዉ ካደረጉት በላይ በአራት ኪሎ ያሉትን አምባገነኖች እየሸረሸረቻቸዉ እንዳለ ታየኝ።

«ትፈታለች» ከሚለዉ «መቼ መጄምሪያዉኑ ታሰረች» ወደሚለዉ ሃሳብ መጣሁኝ። እርሷ በሥጋ ብትታሰርም በርግጥ የታሰረችዉ እርሷ እንዳልሆነች ገባኝ። ነጻ ሴት፣ የመንፈስ ነጻነት የተላበሰች እንደሆነች አየሁኝ።

የታሰሩትስ፣ አላወቁትም እንጂ፣ ጨካኝ አሳሪዎቿ መሆናቸዉን፣ በሥጋ ያልታሰሩ በመንፈስ ግን ሲታይ በጥላቻ፣ በእብሪት፣ በጭንቀት፣ በክፋት፣ በዘረኝነት የተተበተቡ የአዉሬነት ባህሪ የተላበሱና ወደፊት ለልጅ ልጆቻቸዉና ለዘራቸዉ አንገት መድፊያ ምክንይት የሆኑ እንደሆነ ታየኝ።

የእድሜ ባለጸጋ የሆኑት አምባሳደር እምሩ ዘለቀ «የኢትዮጵያ እምቤት» ሲሉ ለወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ ያላቸዉን አክብሮትን ፍቅር ገለጹ። የኔዉ አንድ ፍሬ ልጅ «ብርቱካንን እወዳታለሁ» አለች። ብርቱካን ሚደቅሳ ከልጅ እስከ ሽማግሌ፣ ሴቱን ወንዱም በሙሉ ለአንድ የተቀደሰ ኢትዮጵያ አላማ ወደ አንድነት ያመጣች እንደሆነ እናያለን።






Wednesday, June 03, 2009

 

ኢሕአዴግ ከፈለገ ግንቦት ሰባትን ሊያጠፋዉ ይችላል !

ኢሕአዴግ ከፈለገ ግንቦት ሰባትን ሊያጠፋዉ ይችላል !
ግርማ ካሳ
(muziky68@yahoo.com)



እዉቁ አሜሪካዊዉ የሰብዓዊ መብት ተከራካሪና የሰላም ኖቤል ተሸላሚ የነበሩት ቄስ ዶር ማርቲን ሉተር ኪንግ በተናገሩት አባባል ነዉ ጽሁፌን የምጀመረዉ። «እርስ በርስ መከባበርና መዋደድ ካቃተን ሁላችንም እንጠፋለን» ነበር ያሉት፣ እኝህ በሰላማዊ ትግል ዉስጥ እራሳቸዉን በ39 አመታቸዉ ስዉተዉ፣ አራት ልጆችን አባት አልባ አድርገዉ ያለፉት፣ ታላቅ ሰዉ።

ሰሞኑን የኢትዮጵያ የፖለቲካዉን ደመና ስመለከት ጥሩ ሁኔታ ላይ ያለን አይመስለኝም። ደም ደም እየሸተተኝ ነዉ። የኢሕአዴግ መንግስት በአገሪቷ ያለዉን የፖለቲካ ቀዉስ በሰላም ከመፍታት ይልቅ ተቃዋሚዎችን በሕግ ስም ለመምታት እንዲያስችለዉ «የጸረ-ሽብርተኝነት» ሕግ በሚኒስቴሮች ምክር ቤት አሳልፎ በፓርላማዉ በቅርብ ያጸድቀዋል ተብሎ ይጠበቃል።

በዶር ብርሃኑ ነጋ የሚመራዉ የግንቦት ሰባት ንቅናቄ በበኩሉ በአዲስ አበባ ያለዉን አገዛዝ ሕግ ወጥ የወንበዴ ቡድን ሲለዉ፣ አገዛዙን ለማስወገድ ይረዳዉ ዘንድ፣ አንድ ብሄራዊ የተደራጀ ኢትዮጵያዊ ግንባር (United Ethiopian Command) ለማቋቋም ጥረት ላይ እንዳለ ኢትዮጵያ ሪቪዉ ዘግቧል። እንግዲህ ሁለት ወንድማማቾች ሊተራረዱ ቢላ እየሳሉ እንደሆነ እናያለን።

ሕወሃት ከደርግ ጋር በሚዋጋበት ጊዜ በሃውዜን ትግራይ የተፈጸመዉን ሁላችንም የምናወቀዉ ይመስለኛል። ሕወሃት በዚያ ስብሰባ እያደረገ ሳለ አየር ኃያል ይመጣና ቦምብ ይጥላል። ብዙ የትግራይ ተወላጆች ያልቃሉ። ቦምብ ሲጣልና ንጹሃን ዜጎች ሲያልቁ የሚያሳይ ቪዴዎ ይቀረጻል። ቪዴዎዉን ያየ የትግራይ ተወላጅ ሁሉ ይቆጣል። (እንዴት አየር ኃይል ያን ስብሰባ ሊያዉቅ እንደቻለና በዚያ ቦታ የደረሰዉም እልቂት በተቀናበረ መልኩ በቪዴዮ መቀረጹ የሚያስነሳዉ በርካታ ጥያቄዎች አሉ። ወደፊት በባለሞያዎችና የታሪክ ሰዎች የሚብራራ ይሆናል ብዬ አስባለሁ።)

ይህ የሃዉዜን እልቂት የትግራይ ወጣት ታይቶ በማያታወቅ ሁኔታ ሕወሃትን እንዲቀላቀል አደረገ። የትግራይ ተወላጆች ለመስዋእተነት ቆርጠዉ ሕወሃትን የተቀላቀሉት ዉስጣቸዉ በደርግ ላይ ስላመረረ ነበር። ያመረረ ሰዉ አንዴ ከተነሳ የሚመልሰዉ ነገር የለም።

ታዲያ አሁን የደርግን ቦታ የያዛዉ፣ ከደርግ ይሻላል ብለን የጠበቅነዉ ኢሕአዴግ፣ ዳግማዊ ደርግ ሆኖ፣ እያራመዳቸዉ ባለዉ ጎጂ ፖሊሲዎቹ ብዙዎች እንዲያመሩ እያደረገ እንደሆነ እያየን ነዉ። በተለይም ሰላማዊ በሆነችዋ በወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ ላይ ኢሕአዴግ በወሰደዉ ኢሰብአዊ፣ ኢፍትሃዊና ጨካኝ እርምጃ በርካታ ኢትዮጵያዊያንን በማይፈልጉበት መንገድ እንዲሄዱ አስግድዷቸዋል። በግንቦት ሰባት አካባቢም የምናየዉም ክስተት ይሄንኑ በግልጽ የሚያሳይ ነዉ።

የግንቦት ሰባት ደጋፊ አይደለሁም። በድርጅቱ ላይ በርካታና የጠነከሩ ትችቶችን አቅርቢያለሁ። የግንቦት ሰባት መፈጠር ጎጂ ነዉ ባይ ነኝ። ነገር ግን አንድ መታወቅ ያለበት ነገር አለ።

የግንቦት ሰባት መሪዎች አብዛኞቹ ጠንካራ የሰላማዊ ትግል ታጋዮች ነበሩ። ለዚህም ማስረጃ እንዲሆን ከምርጫ ዘጠና ሰባት በፊትና የዚያን ሰሞን፣ ዶር ብርሃኑ ነጋ ያስተላልፉት የነበረዉን መልዕክት ማዳመጥና ከቃሊቲ እሥር ቤት ሆነዉ የጻፉትን መጽሐፍ ማንበብ እንችላለን። አንድ ጊዜ እንደዉም በስቶክሆልም ባደረጉት ንግግር፣ ለኢሕአዴግ ከበሬታ ሊኖርን እንደሚገባ ዶር ብርሃኑ ሲናገሩ « ወያኔ ማለት የለብን። አክብረናቸዉ፣ እንዲጠሩ በሚፈልጉት ስም ነዉ መጥራት ያለብን። ኢሕአዴግ ነዉ ማለት ያለብን» ብለዉ ነበር። በመጽሃፋቸዉ ላይ እንደጻፉትም ከአቶ በርከት ስምኦን ጋር ጓደኛሞችና አብረዉ ቢራ ይጥጡ እንደነበረም ገልጸዉልናል። ያን ያህል በኢሕአዴግ ላይ አምኔታ የነበራቸዉ እኝህ ሰዉ በግፍ ከሌሎች የቅንጅት መሪዎች ጋር ቃሊቲ ተወረወሩ። ያኔ ኢሕአዴግ ያደረገዉ ግፍ ዉስጣቸዉን ምሬት እንዲሞላዉ ያደረገ ይመስለኛል።

በተመሳሳይ ሁኔታ የቅንጅት ዋና ጸሃፊ የነበሩት አቶ ሙሉነህ እዮኤልም በሰላማዊ ትግል አቋማቸዉ የጸኑ ሰዉ እንደነበሩ የሚታወቅ ነዉ። እርሳቸዉም በቃሊቲ ተወረወሩ። እንደዉም በተለያዩ የመገናኛ ሜዲያዎች እንዳነበብነዉ ለብዙ ጊዜ እንደርሳቸዉ ያኔ በጨለማ ቤት ዉስጥ እንዲቀመጥ የተደረገ አልነበረም። (አሁን ከአምስት ወር በላይ በጨለማ ቤት ያለችዉ ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ በብዙ ወራት በለጠቻቸዉ እንጂ)

አቶ አንዳርጋቸዉ ጽጌ በዝዋይ ከብዙ ሺህ ወጣቶች ጋር ታስረዉ በሰደፍ አይናቸዉን የተደበደቡና የኢሕአዴግን የግፍ በትር ለጥቂት ወራትም ቢሆን የቀመሱ ሰዉ ናቸዉ።

እነዚህ አንድ ወቅት የሰላምዊ ትግል አርበኞች የነበሩ ሰዎች፣ አሁን ተስፋ ቆርጠዉ ወደ ማይፈልጉት የትግል መሥመር ተሰማሩ። እርግጠኛ ነኝ፣ የደረሰባቸዉ እስራትና ግፍ ባይደርስባቸዉ ኖሮ ምናልባት አሁን ወደ ደረሱበት ደረጃ ላይደርሱ ይችሉ ነበር። በደርግ ጊዜ ኢሕአዴግን የወለደዉ የሰፊዉ ህዝብ ብሶት እንደነበረ፣ አሁንም ብሶትና ግፍ የግንቦት ስባት ንቅናቄን ፈጠረ ማለት ይቻላል። የግንቦት ስባት አባት ኢሕአዴግ ነዉ።

አሁን ኢሕአዴግ የግንቦት ሰባትን ጉዳይ አጣጥሎ ሊመለከተዉ ይችላል። ከዚህ በፊት ኮሎኔል መንግስቱ ኃይለማሪያም «አሁን ኢትዮጵያን ነጻ የሚያወጣዉ ወያኔ ነዉን ? » ብለዉ እንዳሾፉት ማለት ነዉ። ነገር ግን የኢሕአዴግ ባላሥልጣናት የግንቦት ሰባትን እንቅስቃሴ መናቅ የለባቸዉም እለለሁ።

እንዳሉት ግንቦት ሰባት ወሬ ብቻ ሆኖ ሊቀር ይቻላል። በተለይም ድርጅቱ የሚያወላዉልና የተጨበጠ አቋም ይዞ የማይራመድ ከሆነ፣ በዉጭ አገር ብቻ በሚደረግ እንቅስቃሴ ዉጤት ማምጣት ከፈለገ፣ በፍሎሪዳ እንዳሉ የኩባ ተቃዋሚዎች ጥርስ እንደሌለዉ አንበሳ ማጓራት ብቻ ይሆናል ሥራዉ።

ነገር ግን ሌሎች ድርጅቶችን አስተባብሮ ጠንካራ ግንባር ከመሰረተ ትልቅ ለውጥ ሊያመጣ የሚችልበት ሁኔታ ሊኖር ይችላል።

በአስመራ ኦነግ፣ ኦብነግ ፣ የአርበኞች ግንባር …የመሳሰሉ ድርጅቶች ለአመታት የትጥቅ ትግል እናደርጋለን ሲሉ ነበር። ኦብነግና ኦነግ አንድ ጎሳ እንወክላለን ስለሚሉ በኢትዮጵያ ህዝብ ድጋፍ ሊያገኙ አልቻሉም። የአርበኞች ግንባር ጠንካራ መሪ አልነበራቸዉ። ስለዚህም የትም ሊደርሱ አልቻሉም።

የግንቦት ሰባት የአመራር አባላት፣ በተለይም በኢትዮጵያ አንድነት ያምናል የተባለዉን በጄነራል ከማል ገልቺ የሚመራዉን ኦነግ ፣ እንዲሁም የአርበኞች ግንባር አቅፈዉ በአረንጓዴ ቢጫ ቀይ ባንድራ ሥር ግንባር ቢመሰርቱ፣ የተመሰረተዉ ግንባር በቀላሉ አለም አቀፍ እዉቅና ሊያገኝ የሚችል ይመስለኛል። በኢትዮጵያዊያንም ዘንድ እነ ዶር ብርሃኑ ነጋና አቶ ሙሉነህ እዮዔል የታወቁ እንደመሆናቸዉ በርካታ ዜጎች፣ የቀድሞ ወታደራዊ መኮንኖች፣ እንዲሁም አሁን በዉትድርና የሚያገለግሉ በቀላሉ ግንባሩን በመቀላቀል ሊያጠናክሩት ይችላሉ።

ይህ ግንብር ሕወሃት ከደርግ ጋር ሲታገል ያደርግ እንደነበረዉ፣ ከአቶ ኢሳያይስ አፈወርቂ ጋር የሚሰራም ከሆነ፣ የጦር መሳሪያ፣ መድሃኒቶች የመሳሰሉትን በቀላሉ ሊያገኝ የሚችልበት ሁኔት ሊፈጠር የሚችል ሲሆን በኤርትራ ወታደሮችን በማሰልጠን ከኤርትራም ሆኖ ከፍተኛ የፖሮፖጋንዳ ዘመቻ በመልቀቀ በአጭር ጊዜ ዉስጥ ጠንካራ ግንባር ሊወጣዉ ይችላል።

በዚህም ሆነ በዚያ፣ አሁን ያለንበት ሁኔታ ካልተሻሻለ፣ ከላይ ለመጠቆም እንደሞከርኩት፣ አገራችን ጦርነት ላይ ተዘፍቃ ከዉርደት ወደ ዉርደት፣ ከድህነት ወደ ድህነት፣ ከሰቆቃ ወደ ሰቆቃ መሄዷ አይቀሬ ነዉ። ምልክቱን እያየን ነዉ። የክተት ዘማቻዎችን እየሰማን ነዉ። እየተሳለ ያለዉ ጎራዴ አንገቱን የሚቆርጠዉን ፈልጎ እያንጸባረቀብን ነዉ።

እንግዲህ ይሄን ሁሉ የምዘረዝረዉ ወደፊት ሊምጣ የሚችለዉን አደጋ በማሳየት አስቀድሞ ለሁላችንም የሚበጀዉንም ሰላማዊ መፍትሄ በጋራ አሁኑኑ ለመፈለግ ወደ ሚያስችለን ደረጀ ሁሉንም ወገኖች በተለይም ኢሕአዴግን ለመግፋት ነዉ። ኮሎኔል መንግስቱ ኃይለማሪያም ወያኔ-ኢህአዴግን ያናንቁ እንደነበረዉ አቶ መለስ ዜናዊም ተመሳሳይ አስተሳሰብ ኖሯቸዉ በጡንቻና በጉልበት፣ ጠመንጃ ያነሱትን እጨፈልቃለሁ ብለዉ የሚያስቡ ከሆነ የደረቁ ዛፎች በሞሉበት ጫካ እሳት እንደለኮሱ ተደርጎ የሚወሰድ ነዉ።

የግንቦት ሰባት ንቅናቄን የወለደዉ ኢሕአዴግ እራሱ ነዉ። የግንቦት ሰባትን ንቅናቄ እያጠናከረ ያለዉ ኢሕአዴግ እርሱ ነዉ። ኢሕአዴግ የግፍ አገዛዙን በጨመረ ቁጥር፣ በኢሕአዴግ ላይ ያለዉ ጥላቻና ምሬት እያደገ ይመጣል። ጥላቻዉና ምሬቱ ደግሞ ሰዉን ወደ ማይፈልገዉ ደረጃ ይወስደዋል። ነፍጥ እንዲያነሳ ያደርገዋል።

እስከአሁን የተደራጀ ኢትዮጵያዊ ኃያል ስላልነበረ ነፍጥ ለማንሳት የሚፈልግ ከነበረ ምንም ማድረግ አልቻለም ይሆናል። ከአሁን በኋላ ግን፣ ከሃዉዜን እልቂት በኋላ የትግራይ ወጣቶች ወደ ሕወሃት ካምፖች እንዳመሩት፣ አሁን ደግሞ የከፋዉና የመረረዉ ወደ ግንቦት ሰባት ፊቱን ያቀናል። (እንደሚወራዉም ከሆነ በርካታ ኢትዮጵያዊያን በተለይም ከጎጃምና ከጎንደር ድንበር እያቋረጡ ኤርትራ እየሄዱም ነዉ)

ይሄንን ነዉ ኢሕአዴግ የሚፈልገዉ ? ጦርነት ነዉ ኢሕአዴግ የሚፈልገዉ ? እነ አቶ መለስ ደርግን ከመጣላቸዉ በፊት ከወጣትነት እድሜ ጀምሮ ጦርነት ላይ ነበሩ። ስባት አመት በስላም ከገዙ በኋላ እንደገና ከኤርትራ ጋር ጦርነት ጀመሩ። እስከአሁን ድረስ በመሰረቱ ከኤርትራ ጋር «ጦርነት» ላይ ናቸዉ ማለት ይቻላል። በሶማልያ ጋር ለሁለት አመት ጦርነት ዉስጥ ነበሩ። እስከ መቼ ይሆን እነዚህ ሰዎች ጦርነትን የሚናፍቁት ? መቼ ይሆን በሰላም መኖር የሚመርጡት ?

እኔን ምክረን ቢሉኝ «ኳሱ በሜዳቹህ ነዉ። ብትፈልጉ በአገራች ያለዉ ችግር በሰላም እንዲፈታ፣ ጦርነት አስከፊ ነዉና አገራችን ወደ ጦርነት እንዳትዘፈቅ ሰላምዊ መፍትሄ እንዲመጣ ማድረግ ትችላላቹህ» ነበር የምናላቸዉ።

«እንዴት ነዉ ወደ ጦርነት ወደ እልህ ወደ መጠፋፋት እየወሰደን ያለዉን ዝንባሌ፣ አቅጣጭዉን መቀየር የምንችለዉ ?» የሚል ጥያቄ ሊነሳ ይችላል። አንዳንድ ሃሳቦችን እንደሚከተለዉ ልዘርዝር ፡

መጀምሪያ እኛም ወንዶች ሆነን መተኮስ እንደምንችል ሌሎችም መተኮስ እንደሚችሉ ማወቅ ያስፈልጋል። ማንም ከማን አያንስም።

ሁለተኛ እንደ ኢትዮጵያዉያን ሌሎችን በሕግ ስም «ለምን ነፍጥ አነሱ ? ሽብርተኞች ናቸዉ» ብሎ ከመክሰስ ይልቅ፣ ነፍጥ ያነሱበትን ምክንያት መርምረን ነፍጥ ላነሱበት ጉዳዮች በሰላም በትህታ ዘላቂነት ያለዉን መፍትሄ መፈለግ አለብን።

ሶስተኛ ኢሕአዴግ በርግጥ ግንቦት ሰባትና ሌሎች በርሱ ላይ የተነሱ ድርጅቶች እንዲጠፉ ከፈለገ ቀላል መንገዶች አሉት። ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳን ያለ አንዳች ቅደመ ሁኔታ በአስቸኳይ ቢፈታ፣ በኢትዮጵያ የጠበበዉን የሰላምዊ ፖለቲካ መድረክን ቢያስፈ፣ በሚቀጥለዉ አመት የሚያደረገዉ ምርጫ ነጻና ፍትሃዊ እንዲሆን ሁኔታዎች ቢያመቻች፣ ለአገሪቷም ለሕዝቡም ለራሱም ለኢሕአዴግ የሚበጅ ነዉ ብዬ አምናለሁ። ኢትዮጵያዉያን በሰላማዊ ትግል ላይ ያላቸዉ እምነት ይጨምራል። እንደ ግንቦት ሰባት አይነት ድርጅቶችን ከመደገፍ ይቆጠባሉ። (ምናልባትም የግንቦት ስባት መሪዎችም እርሳቸዉ «ነገሮች ተስተካክለዋል» ብለዉ ድርጅታቸዉን በራሳቸዉ ፈቃድም ሊያከስሙትና የሰላምዊዉን ትግል እንደገና ሊቀላቀሉ ይችሉም ይሆናል)

ኢሕአዴግ በጭፍን፣ እልህ የተሞላበት፣ ግትርና ኋላቀር ፖለቲካ ተያዘ እንጂ፣ ግንቦት ሰባትን ለመምታት ከሚያወጣዉ የጸረ-ሽብርተኝነት ረቂቅ ሕግ ይልቅ የአንዲቷ የብርቱካን ሚደቅሳ መፈታት መቶ እጥፍ የግንቦት ስባትን ግለት ( Momentum) ሊቀንሰዉ ይችላል።

በርግጥ ግንቦት ሰባት ንቅናቄን እንደወለደዉ ሁሉ ሊያጠፋዉ ይችላል። በጉልበት ግን አይደለም - በሰላም።









This page is powered by Blogger. Isn't yours?