Tuesday, June 23, 2009

 

የታሰሩትስ አቶ መለስ ናቸዉ - በክፋትና በጭካኔ !

ግርማ ካሳ (muziky68@yahoo.com)


ሁለቱም በኢትዮጵያ እየተፋፈመ በመጣዉ የፖለቲካ ሂደት ዉስጥ ትልቅ ስፋራ አላቸዉ። ሁለቱም አባል የሆኑበት ደርጅት ሊቀመንበር ናቸዉ። ሁለቱም በደጋፊዎቻቸዉ ይደነቃሉ። ሁለቱም የሁለተኛ ደረጅ ተማሪ የነበሩ ጊዜ ጎበዝ ተምሪዎች ነበሩ። ሁለቱም የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተማሪ ሆነዋል። ሁለቱም የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸዉን ያጠናቀቁት በአዲስ አበባ ነዉ። ሁለቱም ወላጆች እንደመሆናቸዉ የልጅን ፍቅር ያወቃሉ። ሁለቱም ኢትዮጵያዉያን ናቸዉ።

የመጀመሪዉ አቶ መለስ ዜናዊ ይባላሉ። የአምሳ አራት አመት አዛዉንት ናቸዉ። እናታቸዉ የአዲቋላ (ኤርትራ ተወላጅ) ሲሆኑ አባታችዉ ደግሞ የአድዋ ትግራይ ሰዉ ነበሩ። ሌላኛዋ ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ ናቸዉ። አባታቸዉ የወለጋ ሰዉ ሲሆኑ እናታቸዉ ደግሞ የሸዋ ሰዉ ናቸዉ።

በነዚህ ሁለት የፖለቲካ ሰዎች ዉስጥ ትግራይ፣ ኤርትራ፣ ወለጋና ሸዋን እናያለን። (ከቀድሞ የኢትዮጵያ አሥራ አራቱ ክፍለ ሃገራት አራቱ ማለት ነዉ)

አቶ መለስ ወላጆቻቸዉ ያወጡላቸዉ ስም ለገሰ የሚል ነበር። «ዜናዊ» ማለት ዜና አብሳሪ ማለት ይመስለኛል። ወላጆቻቸዉ ለገሰ ዜናዊ ሲሏቸዉ «የሚያበስር ተሰጠን፣ ተወለደልን፣ ተለገሰን» ብለዉ ሳይሆን አይቀርም ብዬ አስባለሁ። መቼም ወላጆቻቸዉ ያኔ የተመኙት አቶ መለስ(ለገሰ) መልካም ብሥራት፣ መልካም ወሬ እንዲያብሰሩ ይመስለኛል።

ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ ስማቸዉ እንደሚገልጸዉ፣ ወላጆቻቸዉ «ያማረች፣ የጣፈጠች፣ በሰዉ የተወደደች ትሁን» ብለዉ ይመስላል ብርቱካን ያሏቸዉ። «ሚደቅሳ»ም ተመሳሳይ ትርጉም አለዉ። «ሚደቅሳ» በኦሮምኛ ማሳመር፣ ማስዋብ ማለት ነዉ።

የወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳም ሆነ የአቶ መለስ ዜናዊ ቤተሰቦች ሁለቱም ልጆቻቸዉ ትልቅ ደረጃ ደርሰዉ፣ መልካም ነገር አድርገዉ፣ በመልካም ነገር ታዉቀዉ እንዲያልፉ ፍላጎት እንደነበራቸዉ ነዉ እንግዲህ የምናየዉ።

የነዚህ ሰዎች መመሳሰል እዚህ ላይ ያበቃል። አሁን ባለንበት ሁኔታ አቶ መለስ ዜናዊ ትልቅ ጭካኔ የተሞላበት ኢሰብአዊ ሥራ በሰላማዊ ዜጎች ላይ እስኪሰሩ ድረስ በጥላቻና በክፋት የተሞሉ እልኸኛ ሰዉ እንደሆኑ እያሳዩ ናቸዉ።

ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ «ቅንጅት የሰዉ ጠላት የለዉም። ወያኔ ጠላት አይደለም። ለአገራችን መፍትሄ ፍቅር ነዉ። ያሰሩኝን ይቅር ብያለሁ» እስከማለት ድረስ በፍቅርና በደግነት የተሞሉ፣ የበደሏቸዉንና ወደ ሁለት አመት ገደማ በግፍ ያሰሯቸዉን ሰዎች ይቅር ያሉ ሰዉ ናቸዉ። አንድ ልዩነት በሉልኝ።

አቶ መለስ ዜናዊ በሚቆጣጠሩት የደህንነት ጽ/ቤት፣ የፌደራል ፖሊስና የአጋዚ ጦር ይመካሉ። እነዚህን ሕሊና የለሽ ሰዎች በመላክ በመቶ የሚቆጠሩ ዜጎችን በጠራራ ጸሃይ አስገድለዋል። በመቶ ሾህ የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያንን በግፍ አሳስረዋል። ሰላማዊ መንደሮችን እንዲቃጠሉ አስደርገዋል።
ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ የታጠቀ ሰራዊት የላቸዉም። በቤታቸዉ መሳሪያ አልተገኘም። በእጆቻቸዉ የወደቀዉን ያነሳሉ እንጂ የቆመዉን ተኩሰዉ አይጥሉም። የሚተማመኑት በሕዝብ ጉልበት እንጂ በጠመንጃ አይደለም። ሁለተኛ ልዩነት በሉልኝ።

አቶ መለስ ዜናዊ በተደጋጋሚ እርሳቸዉንና ደጋፊዎቻቸዉን ትዝብት ዉስጥ እስኪከቱ ድረስ የሚዋሹ ቀጣፊ ሰዉ ናቸዉ። ለምስሌ የቅንጅት መሪዎች ከሁለት አመታት በፊት በተፈቱ ጊዜ አቶ መለስ « ከአሁን በኋላ ወደ ፊት እንጂ ወደ ኋላ መመለስ የለብንም። ሕግን እስካልጣሱ ድረስ (የተፈቱት እሥረኞች) ሙሉ የፖለቲካ መብታቸዉ ተጠብቆ መንቀሳቀስ ይችላሉ» ነበር ያሉት። ነገር ግን ታሪካቸዉን ለዉጠዉ፣ ቀድሞ ከተፈቱት እሥረኞች መካከል ወ/ት ብርትካን ሚደቅሳ በግፍ እንድትታሰር ፈቅደዋል።

ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ ያላደረጉትን «አድርጊያለሁ» እንዲሉ፣ እንዲዋሹ ግፊትና ዛቻ ቢደረግባቸዉም «እምቢ» ብለዉ ለእዉነት የቆሙ ሰዉ ናቸዉ። ለእዉነትም በመቆማቸዉ ትልቅ ዋጋ በአሁኑ ወቅት በመክፈል ላይ ይገኛሉ። ሶስተኛ ልዩነት በሉልኝ”አቶ መለስ ዜናዊ ከቀድሞ የ66ቱ አብዮት ዘመን ከነበረዉ፣ እርስ በርስ በደም ከተቃባዉ ፣ እምነተ ቢስ ፍልስፍናን ለኢትዮጵያ ህዝብ ካስተዋወቀዉ፣ አገራችንን ወደ ጨለማ ከወሰደዉ ትዉልድ ናቸዉ። ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ በጥላቻና በቂም በቀል ካልተሞላዉ ከአዲሱ ትዉልድ ናቸዉ። አራተኛ ልዩነት በሉልኝ !

ምንም ቢሆን ክፉ የሰራ ሰዉ በመንፈሱ ሰላም ስለማያገኝ ፣ አቶ መለስ ዜናዊ የጭንቀትና የመንፈስ ረብሻ፣ የፍርሃት እሥረኛ ሆነዉ እየተሰቃዩ ናቸዉ። እራሳቸውን ይፈራሉ። አብረዋቸዉ ያሉትን የፖሊት ቢሮ አባላት ይፈራሉ። ህዝቡን ይፈራሉ። (ምናልባት የማይፈሩት ጎርደን ብራዉንና ሲልቪዮ ቤሎስኮኒን ብቻ ሳይሆን አይቀርም።) ሌሊት፣ በቤተ መንግስትም በላጠጠ መኝታ ላይ እየተኙ እንቅልፍ የላቸዉም። ለዚህ ሳይሆን አይቀርም ነገሮችን ለመርሳት ያስችል ዘንድ ሲጋራና ጫት አረቄና ካቲካላ የአራት ኪሎን ቤተ መንግስት የሞላዉ። አላወቁትም እንጂ የታሰሩትስ አቶ መለስ ዜናዊ እራሳቸዉ ናቸዉ ። በክፋትና በጭካኔ !

ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ በመንፈሳቸዉ ነጻ የሆኑ ሴት ናቸዉ። በሥጋ በማይመች ቦታ ታስረዋል። ግን በዚያ በማይመች ቦታ ሆነው የጣፈጠ እንቅልፍ ይተኛሉ። ዉስጣቸዉ በፍርሃት የተሞላ አይደለም። በራሳቸዉ ይተማመናሉ። ከማንም ጋር መኖር ይችላሉ። በየትም ቦታ ቢሄዱ ማንም አይነካቸዉ።አምስተኛ ልዩነት በሉልኝ!

እግዚአብሄር አቶ መለስን ከመነፈሳዊ እሥራት ወ/ት ብርቱካን ሚድቅሳ ደግሞ ከሥጋ እሥራት ይፍታቸዉ !

Comments: Post a Comment



<< Home

This page is powered by Blogger. Isn't yours?